06/05/2026
በሐረሪ ክልል 7ኛው አገራዊ ምርጫ ሰላማዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ የዝግጅት ስራዎች እየተከናወኑ ይገኛል
በሐረሪ ክልል 7ኛው አገራዊ ምርጫ ሰላማዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ዝግጅት እየተደረገ መሆኑ የክልሉ ሰላምና ጸጥታ አስተዳደር ቢሮ ገለጸ
የሀረሪ ክልል ሰላምና ፀጥታ አስተዳደር ቢሮ ኃላፊ አቶ ቶፊቅ መሀመድ እንደገለጹት የማህበረሰቡን ተሳትፎ በማሳደግ ሰላምን ማጠናከር ያስቻሉ ስራዎች ተከናውነዋል።
እንዲሁም በክልሉ የፀጥታ መዋቅር ከማጠናከርና የፀጥታ ስጋት ከማስወገድ አንፃር በትኩረት ሲሰራ መቆየቱን ተናግረዋል።
የጸጥታ ሃይሉ፣ ማህበረሰቡና የሰላም አደረጃጀቶችን ባሳተፈ መልኩ የሚከናወነው የሰላምና የጸጥታ ስራዎች ወደ ተሻለ ደረጃ ማድረስ መቻሉን ተናግረዋል።
በክልሉ በአሁኑ ወቅትም አወንታዊ ሰላም መገኘቱንና ይህንንም ዘላቂ ከማድረግ አንጻር የተቀናጀ ስራ እየተከናወነ ይገኛል ብለዋል።
በተለይ በክልሉ ጸጥታ መዋቅሩ ላይ የተከናወኑት የሪፎርም ስራዎች ለተገኘው ወጤት አስተዋጽዎ ማድረጉን አብራርተዋል።
እንዲሁም ህዝቡን በሰላምና ጸጥታ ስራዎች ላይ በማሳተፍ የሰላሙ ባለቤት እንዲሆኑ በማስቻል ረገድ የተከናወኑት ስራዎችም ውጤት ማስገኝቱን ገልጸዋል።
በዚህም በክልሉ ኮንትሮባንድን፣ ህገወጥ የመሬት ወረራና ግንባት፣ ህገወጥ ንግድና የነዳጅ ሽያጭ በመከላከልና በድርጊቱ የተሰማሩ አካላትን በቁጥጥር ስር እንዲውሉ መደረጉንም አንስተዋል።
በክልሉ 7ኛው አገራዊ ምርጫ በቅድመም ሆነ በምርጫ ወቅትና ከምርጫ በኋላ ሰላማዊ ሆኖ እንዲጠናቀቅ ህዝቡን ያሳተፈ ስራዎች በትኩረት እየተከናወነ መሆኑን አንስተዋል።
የህዝብን ተሳትፎ በማጠናከር የተጀመሩ የሰላምና ጸጥታ ስራዎች ተጠናክረው እንደሚቀጥሉ አቶ ቶፊቅ አክለው ተናግረዋል።