Teppi semaetu qidus giorgis bete kistian

  • Home
  • Teppi semaetu qidus giorgis bete kistian

Teppi semaetu qidus giorgis bete kistian Teppi St.geoge church

የተወደዳችኹ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሃይማኖት ተከታዮች እና የእምዬ ቅድስት ድንግል ማርያም የቃልኪዳን እና የመስቀል ሥር(ዮሐ 19) ልጆች እንደምን ሰነበታችኹ፡፡♥♥እነዚህ ፍሬ የለሽ መናፍቃን ...
22/03/2019

የተወደዳችኹ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሃይማኖት ተከታዮች እና የእምዬ ቅድስት ድንግል ማርያም የቃልኪዳን እና የመስቀል ሥር(ዮሐ 19) ልጆች እንደምን ሰነበታችኹ፡፡

♥እነዚህ ፍሬ የለሽ መናፍቃን ጋር ከምትጨቃጨቁ ለማንኛውም ጥያቄ ኦርቶዶክሳዊ መልስ ሲፈልጉና የተለያዩ አጥጋቢ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ስርዓቷን የጠበቁ ትምሕርቶችን በጽሑፍ እና በድምጽ ለማግኘት ይኽንን የቴሌ-ግራም ቻናሌን ይቀላቀሉ ☞ የተወደዳችኹ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ሃይማኖት ተከታዮች እና የእምዬ ቅድስት ድንግል ማርያም የቃልኪዳን እና የመስቀል ሥር(ዮሐ 19) ልጆች እንደምን ሰነበታችኹ፡፡

♥እነዚህ ፍሬ የለሽ መናፍቃን ጋር ከምትጨቃጨቁ ለማንኛውም ጥያቄ ኦርቶዶክሳዊ መልስ ሲፈልጉና የተለያዩ አጥጋቢ የኦርቶዶክስ ተዋህዶ ስርዓቷን የጠበቁ ትምሕርቶችን በጽሑፍ እና በድምጽ ለማግኘት ይኽንን የቴሌ-ግራም ቻናሌን ይቀላቀሉ ☞

እመቤታችን ስለ ፍቅርሽ የምቆምበትን ቅዱስ ፍቅርሽ እንደ ትናንቱ ዛሬም ይብዛልኝ፡፡

18/02/2019

ላይክ ያድርጉና ይቀላቀሉን

14/09/2016

በስመ አብ ወወልድ ወመንፈስ ቅዱስ አሐዱ አምላክ አሜን፡፡
በክርስቶስ ክረስቲያን በመንፈስ ቅዱስ መንፈሳዊያን የተሰችሁ የእግዚአብሔር ቤተሰቦች
የድንግል ማርያም የአሥራት የበርከት ልጆች በወደደንና በመረጠን በአምላካችን በልዑል
እግዚአብሔር ሰላምታ እንደምን ሰነበታችሁ አመላካችን ቢወድና ቢፈቅድ ወቅቱን
በተመለከተ ስብከት ይዘንላችሁ ቀርበናል፡፡ የምናስተውሉበትን ልቦና ልዑል አምላካችን
እግዚአብሔር ቅዱስ መንፈሱን ለሁላችን ያድለን፡፡
ቃሉን የተናገረው ጌታችን መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ አንቀጸ ብፁዓን ተብሎ በሚጠራው
በተራራው ስብከቱ ነው፡፡ የቃሉን ፍቺ ስንመለከት ስለ ጽድቅ የሚስደዱ ብፁዓን ናቸው ማለት ስለ
እግዚአብሔር ፍቅር፣መንግሥት፣ በረከት፣ ረድኤት ብለው ከትውልድ ሀገራቸው ተለይተው ከከተማ
ከሕዝብ ርቀው በምድር የላመ የጣመ ምግብ ሳይመገቡና ሣይጠጡ ለቁመተ ስጋ ብቻ ያገኙትን
ቅጠል የሚመገቡ ይህችን ዓለም የጠሉ አባቶች እናቶች እነሱ የተመስገኑ ቅዱሳን፣ የተመረጡ
ቡሩካን፣ የተለዩ ምስጉኖች ማለት ነው፡፡
1.1 ሰደት መቼ ተጀመረ ?
በዓለመ መላዕክት ነው፡፡ እግዚአብሔር በዕለተ እሑድ ከፈጠራቸው ከሰባቱ ሥነ-ፍጥረታት
ውስጥ መላዕክት ናቸው፡፡ ከፈጠራቸው በኋላ የተሰወረባቸውም የእርሱን አምላክነት ምሀሪነት
ሁሉን ቻይነቱን ይረዱ ያውቁ ዘንድ ተሰወረባቸው፡፡ የመላእከት አለቃ የነበረ ሳጥናኤል እኔ
ፈጠርኳችሁ በማለት ብዙዎችን አሳተ ቅዱስ ገብርኤል እና ቅዱስ ሚካኤል ሃይማኖታችንን እስከ
ምናውቀው ባለንበት እንቁም(ንቁም በበህላዊነ እሰከ ንረክቦ ለአምላክነ) ብለው መላዕክትን
አጽናኑ፡፡ ሳጥናኤልና ከሰማይ ወደዚህ ዓለም(ምድር) ተሰደዱ ስደትም በእዚያን ጊዜ ተጅመረ፡፡
1.2 ሰዎች የሚሰደዱበት ምክንያት
ሀ/የእግዚአብሔርን ትዕዛዝ በመተላለፍ፡- የሁላችን አባት አዳም አትበላ ተብሎ ከተከለክለው
ከዕፀ በለስ በመበላቱ ገነት ከሚያህል ቦታ እግዚአብሔርን ከመሰለ አምላክ ተሰደደ፡፡ ዘፍ 3፥8
ለ/ረሀብ ቸነፈር ሲመጣ ፡- አንደ አባታችን ቅዱስ ያዕቆብ በሀገሩ ለአመስት ዓመት ረሀብ ሆነ
እግዚአሔርም ያዕቆብን በሕልም አነጋገረው ወደ ግብፅ ሀገር ሂድ ብሎ ነገረው እርሱም ተሰደደ
ዘፍ 46፥11
ሐ/ የሰውን ነፍስ በማጥፋት የሚሰደዱ ፡- ነቢየ እግዚአብሔር ሙሴ አደገ ወደ ወንድሞቹም
ወጣ መከራቸውንም ተመለከተ የግብፅ እና አንድ ዕብራዊ ሲጣሉ አገኛቸው ለዕብራዊውም
በማገዝ ግብፃዊውን ገድሎ በአሸዋ ውስጥ ቀበረው፡፡ በሁለተኛ ቀንም ወጣ ሁለት ዕብራዊያን
ሲጣሉ አየ ሙሴም በዳዩን ለምን ባልንጀራህን ትመታዋለህ አለው፡፡ ወንደሙን ሚበድለውን ያም
ሰው በእኛ ላይ አንተን አለቃ ዋስ ዳኛ ማን አደረገህ? ወይስ ግብጻዊውን ትናንት እንደገደለኸው
ልትገድለኝ ትሻለህን? አለው፡፡ሙሴም በእውነት ይህ ነገር ታውቆአልን ብሎ ፈራ፡፡ ፈርዖንም ይህን
ነገር ሰማ ሙሴንም ሊገለው ፈለገ ሙሴ ግን ከፈርዖን ፊት ኰበለለ በምድያም ምድር ተቀመጠ፡፡
ዘጸ 2፥11-16
መ/ ለሰው ልጆች ሰላም አብነት ለመሆን የሚሰደዱት ስደት ነው፡፡ ይህ ስደት የጌታችን እና
የእመቤታችን ሰደት ነው፡፡ ሰለ ጌታችን እና ሰለ እመቤታችን ሰደት ከመነጋገራችን በፊት ስለ ጌታ
ልደት ትንሽ ልበል ጌታችን በቤተልሔም ሲወለድ ቤተልሔም በእሳት አጥር ታጠረች አጋንንትም
ሄደን እናያለን ብለው ቢቀርቡ የብርሃን መላዕክት በእሳት ፍላጻ እያቃጠሉ ሊያስቀርቧቸው
አልቻሉም፡፡ አጋንንትም ለአለቃቸው ለዲያብሎስ ነገሩት ዳያብሎስም በትዕቢት በኪሩቤል አምሳል
4 ተሸካሚዎችን አዘጋጅቶ ተሸክመውት ቤተልሔም ደረሱ ወደ ጌታም መቅረብ አልቻሉም፡፡ ከዚች
ሰዓት ጀምሮ ዲያብሎስ በስልጣኔ ላይ ችግር የፈጠረብኝ ማነው? ብሎ ፈርቶ እየተንቀጠቀጠ
ለአጋንንት ከእኔ የሚሰወር የለም ዓለምን ዙሬ ነገሩን መርምሬ ውጤቱን እስክነገራችሁ ታገሱኝ
አላቸው፡፡ ሁሉን ቦታ አሰሰ ግን አልቻለም፡፡ መጨረሻ ላይ እነድህ በማለት ተናገረ አስከ ዛሬ ድረስ
ከተሰራው ታአምር የሚበልጥ ታላቅ ተአምር ነው አለ ፡፡ ነቢያት ስለ እርሱ ትንቢት የተናገሩለት
በቤተልሔም ተወልዶ ከሆነ መንግሥቴን እነደሚቀማኝ አልጠራጠርም እያለ ተጨነቀ አሁንም ኑ
ሄደን ጠይቀን እንረዳ ብሎ ሠራዊቱን ይዞ ወደ ቤተለሔም መጣ እረኞች እና መላዕክት በአነድነት
‹‹በሰማይ ለእግዚአበሔር ምስጋና ይሁን በምድርም ለሰው የሰላም መሠረት ተጣለ›› እያሉ
ሲያመሰግኑ ሰምቶ ደነገጠ ፡፡ ሉቃ 2፥12-16
ጌታ ሰለመወለዱ ይነግሩት ዘንድ የእስራኤል የኦሪት ምሁራንን አነሳስቶ ጌታ ከድንግል እስኪ
ወለድ ድረስ አትሞትም በአልጋ ላይ ተጣብቀህ ትኖራለህ ተብሎ ከእግዚአብሔር መላዕክት
ትንቢት ወደ ተነገረለት ወደ ካህኑ ስምዖን ሄደው ስምዖን ሆይ አንተ ተስፋ የምታደርገው የዓለም
መድኃኒት የሆነው ክርስቶስ ወደዚህ ዓለም መምጫው ደርሷን? በማለት ጠየቁት፡፡ ስምዖንም
አዎን መምጫው ደርሷልን አላቸው እርነሱም ጊዜው መድረሱን በምን አወቀህ? አሉት ሰምዖንም
ቀድሞ ነቢዩ ኢሳይያስ 7፥14‹‹ ድንግል በድንግልና ትፀንሳለች በድንግልናም ትወልዳለች ስሙንም
አማኑኤል ትለዋለች›› ፡፡ ተብሎ የተነገረውን ትንቢት ተጠራጥሬ ነበር እና ታስሮ የነበረው እጁ
ሰለተፈታ መወለዱን በዚህ አውቃለሁ አላቸው፡፡
ሰይጣንም የእስራኤልን የኦሪት ምሁራንን ቆሞ ይሰማ ነበርና ፈጽሞ ታወከ የተንኮል ባሌቤት
የሆነው ዲያብሎስም በሄሮድስ ልቡና አድሮ ሄሮድስ! የእኔንና የአንተን ስልጣን የሚቀማን ንጉሥ
ተወልዷልና ከተወለዱ 2 ዓመት እና ከእዚያም በታች እደሜ ያላቸውን ሕፃናትን አስገድላቸው
አለው፡፡ ሉቃ 2፥25-27 ጌታችን፣ አመቤታችን ፣ሰሎሜ እና ቅዱስ ዮሴፍ ወደ ግብፅ ተሰደዱ፡፡
‹‹የጌታ መልአክ በሕልም ለዮሴፍ ሄሮድስ ሕፃኑን ሊገድለው ይፈልገዋልና ተነሳ ሕፃኑንና እናቱን
ይዘህ ወደ ግብፅ ሽሽ እሰክነግርህም ድረስ በዚያ ተቀመጥ›› ማቴ2፥13 የሰላም ባሌቤት
አምላካችን ለእኛ ሲል የግብፅን በረሃ እንደ ጋለ ብረት የሚያቃጥለውን አሸዋ እየረገጠ አሳቹን
ዲያብሎስን ረጋግጦ ከእግራችን በታች ጣለልን፡፡ በእርሱ ስደት የእኛ ስደት ተባረከልን ተቀደሰልን፡፡
ፍጥረታት ሁሉ በመንቀጥቀጥ የሚሰግዱለት እነግሣለው አይል ንጉሥ በሄሮድስ ተሰደደ፡፡
1.3 የጌታችንና የእመቤታችን መሰደድ ምክንያቶች (ነጥቦች)
1/ የአዳምን የ5500 ዓመት ስደት ለመሰደድና ለመባረክ ነው ፡፡
2/ ትንቢቱ ይፈጸም ዘንድ ነው፡፡ ‹‹እግዚአብሔር በፈጣን ደመና ተቀምጦ ወደግጽ ይመጣል
፣የግብጽ የእጆቻቸውን ስራውች በፊቱ ይዋረዳሉ ››፡፡ ኢሳ 19፥1 ከግብጽ መመለሱን አስመልክቶ
የተነገረውም ትንቢት ይፈጸም ዘንድ ነው ፡፡ ‹‹ልጄንም ከግብጽ ጠራሁት ›› ፡፡ሆሴ 11፥2 አንሁም
ከግብጽ ወደ ናዝሬት ሄደ ናዝራዊ ይባል ዘንድ ወደ ናዝሬት ሄደ፡፡ ‹‹በኒቢያት ልጄ ናዝራዊ ይባላል
የተባለው ይፈጸም ዘንድ ናዝሬት ወደ ምትባል ከተማ
3/ ጌታ ባይሰደድ ሕፃናቱ ሲገደሉ እሱ ከሞት ቢተርፍ ትስብእቱ (ጌታ ሰው መሆኑ) ምትአት
ነው ብለው እንዳይሰናከሉ ነው ፡፡
4/ አበነት ለመሆን ለጻድቃን ለሰማዕታት ሰደት ለመጀመር እና የእነሱንን ሰደት ለመባረክ
ለመቀደስ ነው፡፡ ሰማዕትነት በሰይፍ መቀላት በእሳት መቃጠለ በመጋዝ መተርተር ብቻ አይደለም
ዓለምን ንቆ ወደ ምድረ በዳ መሰደድም ሰማዕትነት ነው፡፡
ዕብ 11፥37-38 በመጋዝ የሰነጠቁአቸው በድንጋይ የወገሯቸውን በሰይፍም ስለት የገደሉአቸው
አሉ ማቅ፣ ምንጣፍና ሌጦ ለብሰው ዞሩ፣ ተጨነቁ፡፡ ዓለም የማይገባቸው እነዚህ ናችው፡፡ ዱር
ለዱር ተራራ ለተራራ፣ ዋሻ ለዋሻ ፈርኩታ ለፍርኩታ ዞሩ፡፡
5/ የጌታችን የእመቤታችን መሰደድ የቅዱሳን ሰደት ተባርኮላቸዋል የሕይወት እርካታን
አገኝተዋል፡፡ ጌታችን በስጣ በምትባል ሀገር እመቤታችን ውኃ እና ቁራሽ እንጀራ ለመነች
የሚሰጣት አንድም ሰውም አላገኘችም ሁሉም አባረሯት፡፡ ጌታችን በዓለት ላይ በመስቀል አምሳል
ባርኮ ውኃን አፈለቀ ይችም ውኃ ሁለት ጠባይ ሆነች በእዚያች ሀገር ለሚኖሩ ሰዎች መራራ ከሩቅ
ለሚመጡ ነጋደውች ከማር የበለጠች ጣፋጭ ሆነችላቸው፡፡ የሕይወትን ውኃና ምግብን ዳግመኛ
የማያስርበውን የሚሰጠውን ጌታችን ከለሉት እነዚህ ሰዎችም 2 ጠባይ ካላት ጠጥተው
መረራቸው፡፡ ራዕ 21፥ 6-7 ‹‹ባለማውቅ ጠጥተው ዳግመኛ የሚያስጠማውን ውኃ የዚች
ሀገር ሰዎች ከለከሉት››
እርስ በእረሳችን እንከባበር እግዚአብሔርን ደስ የሚያሰኝ ሥራ እንሠራ ርኅራኄን በጎነትነን
ሀበቶቻችን እናድርጋቸው በረከትን ለማገኘት እግዚአብሔርን እንፈልገው ት.ሶፎ 2፥3
እግዚአብሔርን ፈልጉ ፍርድንም አድርጉ ጽድቅንም ፈልጉ፡፡ ዕብ 12፥4 ‹‹ኃጢአትን ተጋደሏት
አሸንፏትም ፣ተስፋችሁንም የምታሰጣችሁን ትምህርት ውደዷት››፡፡
- ‹‹ኃጢአትን የምትሠራ ነፍስ እርስዋ ትሞታለች ››ት..ሕዝ 18፥ 4
እመቤታችን ስደቷን እያሰብን አንማጸናት ከቦታ ቦታ በመንገላታትሽ ኀዘን የደረሰበት ኀዘን ያውቃልና
ፈጥነሽ ጎብኝን አረጋጊን፡፡
ከእመቤታችን ከስደቷ ተካፋይ ከበረከቷ ተሳታፊ እንዲያደርገን አምላካች ልዑል እግዚአብሔር
ቀዱስ ፍቃዱ ይሁንልን በተማርነው ትምህርት 30፣ 60 እና 100 ያማረ ፍሬ አፍርተን የስሙ
ቀዳሾች የክብሩ ወራሾች አንዲያደርገን ቅዱስ ፍቃዱ ይሁንልን፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር ወወላድቱ ድንግል ወለመስቀሉ
ክቡር

10/09/2016

«ርትዕት ይእቲ ሃይማኖቶሙ ለቅዱሳን አበዊነ ( የአባቶቻችን ሃይማኖት የቀናች
ናት)»፡፡
የንግግርና ሥነ ጽሕፈት ሙያን የተካኑ ምሁራን በትምህርት ጌጣቸው እንደሚሉት «ውሃን
ከጥሩው ሲቀዱት፣ ነገርን ከሥሩ ሲያመጡት» ውሃው ጠጭውን፣ ነገሩም ሰሚውን
ያረካዋል፡፡ በዚህ እውነተኛ ሃይማኖትን ከጊዜው ስመ መሳይ ኑፋቄና የለየለት ክሕደት
ለይቶ በሚያሳይ ትምህርታችን «አበዊነ = አባቶቻችን» ያልናቸው እነማን እንደሆኑ
በጥቅል ማመልከት እንወዳለን፡፡ የቃሉን ዐይነ ምስጢር ቁልጭ አድርጎ ለመግለጽ ያህል
አባትነት መልክና ይዘቱ፣ ግብርና ዐይነቱ በጣሙን ብዙ ነው፡፡ ይሁንና እዚህ ላይ
«የቀናች፣ የጸናች ሃይማኖት» ባለቤቶች ብለን በትምህርታችን ርእስ በመሪነት
ያነሣናቸው፡፡
– ከአዳም ጀምሮ እስከ ኖኅ በደብር ቅዱስ የነበሩ አርእስተ አበውን፣
– ከአብርሃም ጀምሮ እስከ ሊቀ ነቢያት ሙሴ የነበሩትን የእግዚአብሔር ሰዎች፣
– አዕይንተ አርጋብ ዐበይት ደቂቅ ነቢያትን፣
ይልቁንም «አንተ ውእቱ ክርስቶስ ወልደ እግዚአብሔር ሕያው = አንተ የሕያው
እግዚአብሔር ልጅ ክርስቶስ ነህ» ከማለታቸው አስከትለው «እግዚኦ ኀበ መኑ ነሐውር
እንዘ ቃለ ሕይወት ዘለዓለም ብከ፣ ወንሕነሰ አመነ፣ ወአእመርነ፣ ከመ አንተ ውእቱ
ክርስቶስ ወልዱ ለእግዚአብሔር ሕያው = አቤቱ! የዘለዓለም ደኅንነት የሚገኝበት
ትምህርት ከአንተ ዘንድ እያለ ወደማን እንሔዳለን? እኛስ የሕያው እግዚአብሔር ልጁ
ክርስቶስ እንደሆንህ ዐውቀን አምነናል» ማቴ.16-16፣ ዮሐ. 6-68-70 ብለው
መስክረው ሲያበቁ ሃይማኖትን አብርተው ያረጋገጡ፣ ሁለንተናቸው በደመ እግዚእነ
ኢየሱስ ክርሰቶስ ተኮልቶ የበራ፣ የጠራ ጽሩያነ አዕንይት የትምህርት፣ የሃይማኖት፣
የክህነት አባቶቻችን የሆኑ፣ በመንፈስ ቅዱስ ተቃኝተው የተሟሟቁ ቅዱሳን ሐዋርያትን
ነው፡፡
ደግሞም የእነርሱን ዓላማና ግብር የተከተሉ ሰብአ አርድዕትና ምሉአነ አእምሮ ሠለስቱ
ምእት ሊቃውንትን፣ ተጋዳልያን ሰማዕታትና ጻድቃን፣ ቅዱሳን ማለታችን ነው፣ እንጂ
የመጀመሪያው የወንድሙ ነፍሰ ገዳይ የቃኤል ልጆችን ሁሉ አደባልቀን፣ ነገርን ከነገር
አጣልፈን፤ ምስጢሩንም ደብቀን፣ ከሐድያን፣ ጣዖት አምላኪዎች መስሕታንን ቀደምት
አበው ከሆኑ ብለን ሳናስተውል በጅምላው አይደልም፡፡ ስለይህ የእነዚህን ቅዱሳን =
የተለዩ አበው የቀናች፣ የጸናች ሃይማኖት የሆነችው «ርትዕት ይእቲ ሃይማኖቶሙ
ለቅዱሳን አበዊነ = የአባቶቻችን ሃይማኖት የቀናች የጸናች ናት፡፡» በዚች መሠረትነት
ለሁለት ሺኽ ዘመናት እምነቷ፣ ሥርዐቷ፣ ባህሏ ተጠብቆ ለሕዝበ ክርስቲያን የሚገባውን
መንፈሳዊና ሐዋርያዊ፣ ማኅበራዊም አገልግሎት ስታቀርብ የኖረች ጥንታዊት፣
ሐዋርያዊትና ብሔራዊት የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን በየዘመናቱ
የገጠሙአትን ችግሮች፣ ፈተናዎች በታላቅ ትዕግሥት፣ በጾምና በጸሎት፤ በመንፈሳዊ
ጥበብ የማለፍ ልምድና ዕውቀቷ በዓለም የተመሰከረ ነው፡፡ ይሁን እንጂ በአለንበት ጊዜ
እምነቷን፣ ሕጓንና ሥርዐቷን ለማፋለስ በግልና በቡድን የተነሣሡ የእምነት ተቀናቃኞች
በየአቅጣጫው በመዝመት ላይ መሆናቸው ለሕዝበ ክርስቲያን ግልጽ እየሆነ መጥቷል፤
አሁንም የበለጠ ሊታወቅ ይገባል፡፡
የመናፍቃንና የሃይማኖት ለዋጮች እንቅስቃሴ በቤተ ክርስቲያን ታሪክ ያልተለመደና
እንግዳ ነገር አይደለም፡፡ ቀድሞ የነበረ፣ ያለና ወደፊትም የሚኖር ነው፡፡ ምክንያቱም
አዝማቹ ጠላት በሞተ ሥጋ የማያርፍ ዲያብሎስ እንደሆነ በብሩህ ልቡና ይታወቃል፡፡
በመልካም እርሻ /ማሳ/ የተዘራው ንጹሕ ስንዴና ጠላት ጨለማ ለብሶ በስንዴው ማሳ
ላይ የበተነው እንክርዳድ እስከ መኸር ጊዜ ዐብረው እንደሚኖሩ ጌታችን ራሱ ባለቤቱ
በቅዱስ ወንጌል አስተምሮናል ማቴ. 13-24 – 31 ይህ የማይሻር ቃል ስለሆነ ሌላ
ምን ይባላል? ዐይነ ኅሊናችንን ወደ ቀደመው ታሪክ ስናቀና በአበው ሐዋርያት ዘመንም
በመልካም እርሻ ላይ በብርሃን የተዘራውን ጥሩ ዘር፣ ለማበላሸት የጥፋት ዘር በጨለማ
የሚበትኑ ቢጽ ሐሳውያንና መናፍቃን ቤተ ክርስቲያንን ሲያውኩና ሲያምሱ ኖረዋል፡፡
በቀና ሃይማኖት ስምና ጥላ ተሸፍነው ትክክለኛውን እምነትና መሠረት ለማፋለስ
ከማሴርም ዐልፈው ራሳቸውን በአማልክት ደረጃ በማስቀመጥ ሰዎችን ወደ ጥፋት
በሚያደርስ መንገድ ለመምራት የቃጣቸው ብዙዎች ነበሩ፡፡ ዳሩ ግን ሁሉም እንደገለባ
እሳት ብልጭ እያሉ ጠፍተዋል፡፡ በዓለም ላይ የበተኑት የጥፋት ዘር ግን ክሕደት
የሚያብብበት ካፊያ ባካፋ ቁጥር በምንጭ ላይ እንደወደቀ ዘር በፍጥነት ይበቅላል፡፡
የእውነት ፀሐይ ስትወጣ ደግሞ መልሶ ይጠወልጋል፡፡ እንደነ ይሁዳ ዘገሊላ፣ እንደነ
ቴዎዳስ ዘግብጽ የመሳሰሉት ከብዙዎች በምሳሌነት ሊጠቀሱ ይችላሉ፡፡ «ቴዎዳስ
ዘግብጽ» አምላክ ነኝ ብሎ ተነሥቶ እሰከ አራት መቶ የሚደርሱ ተከታዮች አፍርቶ ነበር፡፡
ይሁን እንጂ ብዙ አልተጓዙም እርሱም፣ ተከታዮችም ፀሐየ ጽድቅ ሲወጣ
እንደሚጠወልገው ሣር ፈጥነው ጠፍተዋል፡፡ ይሁዳ ዘገሊላም እንደዚሁ ነው፡፡ አልቆየም፤
ጠፍቷል፡፡ /ግ.ሐ. 5-37/
ጥንታዊት ሐዋርያዊት ብሔራዊት ቤተ ክርስቲያናችንን ለመበታተን የሚጥሩት ሁሉ
መሠረቷ በክርስቶስ ደም የጸናውንና በቅዱሳን አባቶቻችን ዐፅም የታጠረችውን ቤተ
ክርስቲያን ሲገፏትና ሲነቀንቋት ፈተናውን በትዕግሥት በማስተዋልና በትምህርት
በመከላከል ትቋቋመዋለች፡፡ ይህ የብዙ ዘመን ልማዷ ነው፡፡ መቼውንም ቢሆን ግራ
አያጋባትም፡፡
አባቶቻችን ያቆዩን የኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ሃይማኖት ጥንታዊት የቀናች፣ የጠራች፣ ስለሆነች
ተካታዮቿን የምታኮራ እንጂ የምታሳፍር አይደለችም፡፡… በሰዎች የግል ድካም እንጻርም
አትመዘንም፡፡ ለመከራም አትበገርም፡፡ ቤተ ክርስቲያናችን እስከ ዛሬ ድረስ በእምነቷ፣
በጾሟና በጸሎቷ የማያቋርጥ የገቢረ ተአምራት ወመንክራት፣ ኀይላትም ሥራ ስትሠራ
የምትገኝ ለተከታዮቿ ተስፋ ሆና የምትኖር እውነተኛ ቤተ ክርስቲያን ናት፡፡ ርግጥ ነው፤
በቅን ልቡናና በትሑት ሰብእና ለተቀበለው ሸክሟ ቀላል ቀንበሯ ልዝብ ነው፡፡ ዳሩ ግን
በገድል የተቀመመ ሕጓ፣ ባህሏና ሥርዐቷ ጥብቅ ስለሆነ የሕግና የሥርዐት ቀንበር
ላለመደ ስስ ጫንቃ አይመችም፡፡ መንገዱ ቀጭን፣ በሯ ጠባብ ነው፡፡ የእግዚአብሔርም
መንግሥት የምትወርሰው በመከራ መስቀልና ብዙ ትዕግሥት፣ በዚሁ ቀጭን መንገድ
ተጉዞና በጠባቡ በር ዐልፎ ስለሆነ በቀና ሃይማኖት ጸንቶ፣ በጾም በጸሎት ተወስኖ
ሕይወቱን = አኗኗሩን በሥነ ምግባር፣ ገዝቶ በአበው፣ መንፈሳዊ መንገድ መጓዝ
ለክርስቲያን አምላካዊ ትእዛዝ ነው፡፡ ማቴ. 7-13-05 የሐዋ.14-22 ይህ ጠባብ በርና
ቀጭን መንገድ የሃሪካችን መዛባት የለበትም፡፡ ተቆርቋሪዎች እንሁን፡፡ የወይራ ዛፍ
ተቀጥላው ብሳና ቢሆን እጅግ ያሳፍራልና፡፡ በነገረ ጠቢባን «ሳይረቱ አይበረቱ»
ተብሏልና፡፡
ለመሆኑስ አባቶቻችን ታቦት ተሸክመው እየዘመቱ ከጾም ጸሎታቸው ጋር በተጋድሎ
አጥንታቸውን ከስክሰው፣ ደማቸውን አፍስሰው በአቆዩአት ኢትዮጵያ ሀገራችን ነጻነታችንን
ማን ይነካብናል ብለን እንሰጋለን? ሕግ አክባሪነትና ወሰን የሌለው ትዕግሥታችን ካልሆነ
በስተቀር ለመሥዋትነቱ ከቶ የእነማን ልጆች እንደሆን ሊዘነጋ አይገባምና በአካልም
በመንፈስም ስለ ሃይማኖታችን እንበርታ፡፡ የእውነተኛ ሃይማኖት ዐላማው፣ ውጤቱ እስከ
ሞት ድረስ እንኳ ትንሽም አለመፍራት መሆኑን ማስታወስ አለብን፡፡ ት.ዳ.3-13-ፍጻ፡፡
አሁንም እንደ ቀድሞው መንፈሰ ኀይልን ታጥቀን እንነሣ፤ አምላካችን እንደ አባቶቻችን
የኀይልና የጥበብ መንፈስን እንጂ የፍርሀትና የመደንገጥ ሀብትን አልሰጠንምና
በሃይማኖታችን ማንንም አንፍራ፤ አንሸበር፡፡ የዜግነት ግዴታችንን እየተወጣን መብታችንን
ጠብቀን ለማስጠበቅ እንታገል፡፡ 2ጢሞ.1-7፡፡
በሰፊዋ ሀገራችን እንኳን ተወልደው ያሉ ዜጎቿ ቀርቶ ከተለያዩ ሀገሮች የሚመጡ ባዕዳን
ሁሉ በተለያየ እምነታቸው ተከራይተውና ተጎራብተው እንዲኖሩ ቤተ ክርስቲያናችን
አልተቃወመችም፡፡ ከማንኛውም የእምነት መሳይ ተቋም ደልላ የእንጀራ ልጆች
ለማፍራትም አትፈልግም፡፡ ከጅሏትም አያውቅ፡፡ ይህን የሚያደርጉ ግን ሌሎች ናቸው፤
እዚህ ላይ ስማቸው ባይጠራም በዚሁ የሃይማኖት መሳይ ኑፋቄ የደላላነት ግብራቸው
ይታወቃሉ፡፡ ማቴ. 7-15
«የሁሉ ሰው መብትና ነጻነት ሰብአዊ ፍላጎትም ተጠብቆ በእኩልነት እንኑር» የሚለውን
የአስተዳደር መርሕ እንቀበላለን፡፡ አምላካዊ ሕግም ነው፡፡ በሃይማኖት ከማይመስሉን ጋር
ግን በእምነት ጉዳይ መቼም ቢሆን አንድነት የለንም አይስማማንም፡፡ ከይዞታችንና
መብታችን ሌሎች እንዲገቡብንም አንፈልግም፡፡ እኛም ከነሱ የምንሻው ምንም ነገር
የለም፡፡ አይጠቅመንምና፡፡ ይህ ምርጫችን ነው፡፡ ግድ የሚለን የለም፡፡ «ሲኖሩ ልጥቅ፣
ሲሔዱ ምንጥቅ» የሚለው የአበው ምሳሌያዊ ቃለ ኀይል ሥጋችንን ዐልፎ ዐጥንታችንን
በማስተዋል አለምልሞታልና፡፡ ይልቁንም «ብርሃንን ከጨለማ ጋር የሚቀላቅለው
ማነው?» የሚለው ቃለ ቅዱስ መጽሐፍ ጠፈር፣ ደፈር ሆኖ ይከለክለናል፡፡ክርስትናችንን
ይበርዝብናል ክልክል ነው፡፡ 2ኛቆሮ.6-14-ፍጻ፡፡ ይህን በጥሞና እንገንዘበው፡፡ እኛ
ሃይማኖት መጽደቂያ፣ ምግባረ ሃይማኖት ማጽደቂያ እንጂ የሥጋ መተዳደሪያ እንዳልሆነ
በውል ስለምናውቅ የሃይማኖትን ጉዳይ ከማናቸውም ሥጋዊና ጊዜያዊ ደስታ ጥቅም
ጋር አናያይዘውም፡፡. . . ለዚህም ብለን ሃይማኖትና ሥርዐታችንን አንሸጥም፤
አንለዋውጥም፡፡ ይህ የቅዱሳን አበው ትውፊታችን ነው፡፡ ከደማችን የተዋሐደ
ክርስቲያናዊ ጠባያችንም ይኸው ነው፡፡ ሮሜ12-18 ነገር ግን ይህ አቋምና ጠባያችን
ከሞኝነት ተቆጥሮ ያላችሁን ሁሉ እንቀማችሁ እንቀስጣችሁ የሚሉንን አምረን
እንቃወማለን፡፡ ይገባናልም፡፡ ብዙዎች የእምነት ተቋሞች ሳይሆኑ ነን ባዮች የታሪክና
የሃይማኖት መሠረታቸውን እየለቀቁ፣ የነበራቸውን ትውፊት በቁሳቁስና በኃላፊ ጥቅም
እየለወጡ ባዶ እጃቸውን ስለቀሩ እኛ ከቅዱሳን አበው ወርሰን ጠብቀንና አጥብቀን
የያዝነውን ነፍስ እንዳላወቀ ሕፃን «ካክሽ» እያሉ በማስጣል እኛነታችንን ሊአስረሱን
ይፈልጋሉ፤ አልፈው ተርፈውም ወቅትንና አጋጣሚን ዐይነተኛ ተገን /መሣሪያ/ በማድረግ፣
ነገሮችንም ከፖለቲካና ከግዚያዊ ችግር ጋር በማስተሳሰር የሕዝብን አስተያየት
ለማዘናጋትና የመብታችን ተካፋዮች ለመሆን መስለው ይቀርባሉ፡፡ ከሃይማኖት መሳይ
ቤተሰባቸው ለጊዜያዊ ችግር የሚገኘውን ጥቂት ርዳታ የሃይማኖት፣ የታሪክና የቅርስ
መለወጫ ሊአደርጉትም በእጅጉ ይሻሉ፡፡
እውነተኛው የኢትዮጵያ ሕዝብ ግን «ኩራት እራቱ» ስለሆነ እንደኤሳው ብኩርናውን
በጊዜያዊ ጥቅም /ነገር/ አይለውጥም፡፡ «ነብር ዥንጉርጉርነቱን» እንደማይለውጥ
የኢትዮጵያ ሕዝብም፣ ለሃይማኖቱ፣ ለክብሩ፣ ለታሪኩና፣ ለነጻነቱ መሞት እንኳ የተለየ
መታወቂያው፣ የማይለወጥ ጠባዩ ነው፡፡ ኤር. 13-23፡፡
በዐያሌው ከልብ የተወደዳችሁ፣ እውነቱ ያልተሰወራችሁ የቤተ ክርስቲያን አባላት ሆይ!
የእምነታችሁና ሥርዐታችሁ ጠባቂዎች፣ የቤተ ክርስቲያናችን ሕይወቷ ደስታዋና ክብሯ
ተከታዮቿ እናንት ምእመናን ስለሆናችሁ ልጆቻችሁና ወዳጆቻችሁ በዐዲስ የሃይማኖት
ትምህርት መሰል ክሕደት እንዳይወስዱ ጊዜና ቦታ በማይገድባቸው ወደ ጥፋት
በሚወስዱ ሰፋፊ መንገዶች ከሚመሩ አዘናጊዎች መናፍቃንና ቢጽ ሐሳውያን መምህራን
እንድትጠበቁ፣ «ዐደራ»! ትላችኋለች እናታችሁ ቅድስት ቤተ ክርስቲያን፡፡ ደግሞም
በቅዱሳን አበው ሃይማኖታችሁ እንድትጸኑ ታሪካችሁን፣ ሀገራችሁን ባህላቸሁን፣
ፍቅራችሁን፣ አንድነታችሁን ጠብቃችሁ በጥንቃቄና በሥርዐት እንድትኖሩ፣ እኛም እጅግ
ጥብቅ የሆነ መንፈሳዊ ፍቅር የተመላ መልእክታችንን በእናት ቅድስት ቤተ ክርስቲያን
ሕያው ስም ከቅን ልቡና በመነጨ ሐሳብ አናስተላልፋልን፡፡ 1ቆሮ.14-15
መድኀኒታችን እንዳስጠነቀቀው ከሐሰተኞች መምህራን ተጠበቁ፤ የዘመኑን ምትሐታዊ
ሒደትና ይዘት ዕወቁ፤ በመንፈሳዊ ሕይወት ጽኑ፡፡ በተለያዩ የተፈጥሮና ሰው ሠራሽ
ችግሮች ምክንያት ከዓለም ኅብረተሰብ የምናገኘው ጊዜያዊ ርዳታ በሰብአዊና ማኅበራዊ
ግዴታ ላይ የተመሠረተ እንጂ የሃይማኖትና የታሪክ ለውጥ መዋዋያ አይደለም፡፡
የመልካም ጠባይና ማንነት መለወጫም አይደለም፡፡ ድኽነትን ከየቤታችን ለማጥፋት
ሥራን እንውደድ፡፡ እርስ በርስ እንረዳዳ፡፡ ችግረኛውን ተባብረን ነፃ እናውጣው፡፡
እንደቀሞው ባህላችን ያለንን ተካፍለን ዐብረን እንብላ እንጂ መነፋፈግን አንልመድ፡፡
በዚህ ጊዜ የበረከት አምላክ ረድኤት በረከቱን ይሰጠናል፡፡ ወገንና መጠናችንንም ለይተን
ዕንወቅ እንጂ የቅዱሳን አበው ልጆች እዚህ ላይ አትኩረን ልብ እንበል፡፡ በምንም ሰበብ
እንደ ገደል ውሃ ክንብል አንበል፡፡ ይህን ከመሰለው ደካማ ሐሳብም ልጆቻችሁን በብዙ
ዘዴ ጠብቁ፡፡ የሃይማኖት ፍቅር ቁም ነገሩም ከቤተሰብ በላይ ስለሆነም ይህን አትርሱ፡፡
ምንም ቢሆን ክፉን ማስወጣት ያቃተው ስንኳ ቢኖር መውጣት አያቅተውም፡፡ ማቴ.
10-36-40
በቤተሰብ አባላት በወዳጅ ዘመድና በጎረቤት መስለው የሚመጡ የበግ ለምድ ለባሾችን
ዕወቁባቸው፡፡ ፊልጵ. 3-2 ዋናው ዘዴ ከእነርሱ ጋር ዐብሮ አለመራመድ፣ ዐብሮ
አለመገኘት ነው፡፡ ከደጃቸውም አለመቆም ነው፡፡ የእነርሱ የሆነንም ሁሉ አለመከጀል፣
ፈጽሞ አለመንካት ነው፡፡ የጠላት ገንዘብ ምግብ፣ ልብስና ቁሳቁስ በሙሉ የተወገዘ፣
እርኩስ ነው፡፡ ሕርም ነው፣ መርዝ ነው፡፡ ደዌ ክሕደትን ያመጣል እንጂ ጤና ሕይወት
አይሆንም፡፡ እንወቅ፡፡ በሌላ በኩል በእውነቱ ከሆነ አንድ ልጅ እናቱ መልካም ፍትፍት
ምግብ አዘገጅታ ባትሰጠው እንኳ ከጎረቤት ሔዶ በመርዝ የተቀመመ ምግብ መብላትና
መታመም፣ ዐልፎም መሞት የለበትም፡፡ እንደዚሁም ታዲያ በሥራዋና በመልካም አቋሟ
ሁሉ እንደ መማር፣ ባይሆንም እንደ መጠየቅ «እናቴ ቤተ ክርስቲያን ጮኻ ባታስተምረኝ
ነው» እያሉ ከክሕደትና ኑፋቄ ማኅበር እንደ እሳት ራት ዘሎ መግባት አግባብ አይደለም፤
የሰውነት መመዘኛም አይሆንም፡፡ እንግዲያውስ ተጠበቁ፡፡ ተጠንቀቁ፤ ሌላ የሚያዋጣ
ነገር ፊጽሞ አይገኝም፤ ዐጉል መዋተት ብቻ ይሆናል፡፡ በዚህ ዐዲስ ዘመን ዐዳዲስ
የሃይማኖት መሳይ ድርጅት የቀናች አንዲት እውነተኛ የአበው ሃይማኖትን ሊተካት ቀርቶ
ሊመስላት አይችልም፡፡ ይህን የመሰለው ሐሳብ የዘባቾች ከንቱ ዘበት ነው፡፡
ሰው ሆኖ በተዋሕዶ ተገልጾ በባሕርይ ክብሩ ያለ መድኀኒታችን የባሕርይ አምላክ ኢየሱስ
ክርስቶስንም ከባለቤቱ እንደባዘነ የቤት እንስሳ በዚህ ዘመን በየሜዳውና በየግል
አጋጣሚ «አገኘሁት» አይባልም፡፡ ድፍን ያለ ሐሰት ነው፡፡ እናስተውል፡፡ ወይም
እራሳቸውን እንኳ በማያውቁ ልሙጥ ማይማን ዘባቾች «ተቀበሉት» የሚባልለት ቁስ
አካል፣ አልያም ማደሪያ የሌለው ባይተዋር አይደለም፡፡ ዓለምን በእጁ የያዘ እርሱ በእኛ
የሚወሰን ይመስል የተለያየ ችግር ባለባቸው፣ ተግባር ሥጋዊን በጠሉ፣ የዕለት ምግብ
ፈላጊዎች ልንጎተትና በእነርሱ ዐቅም ተታለን በየዛኒጋባው ልንመሰግ የሚገባን ሰብአዊ
ግብር አይደለንም፡፡ አሁንም በሃይማኖት ቁሙ፣ ጠንክሩ፣ ንቁም በተማራችሁትና
በያዛችሁት እውነተኛ ሃይማኖታችሁ ጽኑ፡፡ ባይረዳችሁ እንኳ ከእናታችሁ ቅድስት
ቤተክርስቲያን ተግታችሁ ተማሩ፤ ጠይቁ፡፡ «ርትዕት ይእቲ ሃይማኖቶሙ ለቅዱሳን አበዊነ
= የቅዱሳን አባቶቻችን ሃይማኖት የቀናች፣ የጸናች እውነተኛም ናት» አማራጭ ተለዋጭ
ፈጽሞ የላትም፤ ዘለዓለማዊት ናት፡፡ በባዕድ ዘመን አመጣሽ ትምህርት እንዳትወሰዱ
አሁንም፣ ምን ጊዜም ተጠበቁ፤ ዕወቁ፤ ተጠንቀቁ፡፡ በቃለ አበው ሐዋርያት
ተገዝታችኋል፡፡ ስለእውነተኛዋ ሃይማኖታችሁ በየትና በማን እንደምትማሩ ለይታችሁ
አስተውሉ፡፡ ተረዱም፡፡ በቀናች ሃይማኖታችሁ ጸንታችሁ በሰላም በብርታት እንድትኖሩም፣
ለጸሎትና ምህላ ትጉ በሥራችሁ ሁሉ እንዳትሰናከሉም፣ እንቅፋታችሁን «ወአምላከ
ሰላም ለይቀጥቅጦ ለሰይጣን በታሕተ እገሪክሙ ፍጡነ = የሰላም አምላክ ፈጥሮ
ሰይጣንን ከእግራችሁ በታች ይቀጥቅጠው!!!» ኀያሉ አምላክ ኀይል፣ ከለላ፣ ይሁነን፡፡
የእመቤታችን ቅድስት፣ ድንግል ማርያም አማላጅነት፣ የቅዱሳን ጸሎት ግርማ ሞገስ
ይሁነን፡፡ ሮሜ 16-20፣ 1ኛቆሮ.16-13፣ ገላ.1-8፣ ቆላ.2-6-11
ምንጊዜም «ክፉ አይልከፋችሁ፣ ደግ አይለፋችሁ»
ከሊቀ ትጉሃን ኀ/ጊዮርጊስ ዳኘ
በጠ/ቤተ ክህነት የዕቅድና ልማት መምሪያ ም/ሓላፊ
ወስብሐት ለእግዚአብሔር
አምላከ ሰማያት ወምድር

01/09/2016

+++ድንግልን አለማመስገን....+++
የድንግልናሽን ኃይል የሚሰድብ ፣ ያለዘር ያለሩካቤ ጸንሰሽ እንደ ወለድሽ የማያምን ርጉም ነው፡፡
ከርኩሰት ሁሉ ንጽህት ፣ ከኃጢአትም ሁሉ የጠራሽ እንደ ሆንሽ የማያምን ሁሉ ርጉም ነው፡፡ ከአንቺ
የተወለደ እግዚአብሔር እንደሆነ የማያምን ፣ እርሱንም ከወለድሽ በኋላ በድንልና እንደኖርሽ
የማያምን ርጉም ነው፡፡
የማያከብርሽ ለልዕልናሽም የማይሰግድ ለዘለዓለሙ ርጉም ነው፤ በፍጹም ልቡናው የማይወድሽ
ከትልቅ ሐሳቡም የማያከብርሽ ርጉም ነው፡፡
በከንፈሮቹ የማያመሰግንሽ ፣ በአንደበቱም የማይመርቅሽ ርጉም ነው፡፡ ለክብርሽ የማይሰግድ ፣
ለገናንነትሽ የማይገዛ ዕድል ፈንታው ፣ ጽዋ ተርታው ገሃነመ እሳት ነው፡፡
ድንግል ሆይ! የሚወዱሽ የተወደዱ ናቸው፡፡ ንግሥት ሆይ! የሚያከብሩሽ የከበሩ ናቸው፡፡ ንጽህት
ሆይ! የሚቀድሱሽ ሁሉ የተቀደሱ ናቸው፡፡ ፍሥሕት ሆይ! የሚመርቁሽ የተመረቁ ናቸው፡፡
ልዕልት ሆይ! የሚያደንቁሽ የተደነቁ ናቸው፣ ውድስት ሆይ! ለንግሥትነትሽ የሚገዙ ሁሉ የተባረኩ
ናቸው፡፡
(አርጋኖን ዘሠሉስ ፣ ምዕራፍ ፬ ፣ ከቁጥር 8-14)

17/08/2016

የእምነታችሁ መፈተን ትዕግሥትን እንዲያደርግላችሁ እወቁ፡፡ያዕ1፡2
ቅድስት ቤተ ክርስቲያን የተዋጀችውና የተመሠረተችው መድኃኒታችን ኢየሱስ ክርስቶስ መከራ ተቀብሎ፣ ሥጋውን ቆርሶ፣ ደሙን አፍስሶ ነው፡፡ ሐዋ.2ዐ፥28፡፡ ቅዱስ ጳውሎስ ይህንን ሲገልጽም “በገዛ ደሙ የዋጃትን የእግዚአብሔርን ቤተ ክርስቲያን ትጠብቁአት ዘንድ መንፈስ ቅዱስ እናንተን ጳጳሳት አድርጎ ለሾመባት ለመንጋው ሁሉና ለራሳችሁ ተጠንቀቁ።” ብሏል፡፡ ኢየሱስ ክርስቶስ ቤተ ክርስቲያንን በደሙ ሲዋጅ ጥንተ ጠላት ዲያቢሎስን ድል ነስቶ፣ ምርኮውን መልሶ፣ ሞትን ደመስሶ በመሆኑ ዲያቢሎስ የድል ነሺውን ቤተ ክርስቲያንና ወደ ነጻነት የተመለሱትን ክርስቲያኖች ዘወትር ይፈትናቸዋል፡፡
ቅዱስ ዮሐንስ ወንጌላዊው እግዚአብሔር ኃላፊያቱንና መጻእያቱን በገለጸለት ራዕይ ስለ ዲያቢሎስ ፈተና ሲጠቁም “ዓለሙንም ሁሉ የሚያስተው ዲያብሎስና ሰይጣን የሚባለው ታላቁ ዘንዶ እርሱም የቀደመው እባብ ተጣለ፤ ወደ ምድር ተጣለ ….ለምድርና ለባሕር ወዮላቸው፤ ዲያብሎስ ጥቂት ዘመን እንዳለው አውቆ በታላቅ ቍጣ ወደ እናንተ ወርዶአልና። ዘንዶውም ወደ ምድር እንደ ተጣለ ባየ ጊዜ ወንድ ልጅ የወለደችውን ሴት አሳደዳት።” ዮሐ. ራዕ. 12፥9-17፡፡
ታሪክና መጻሕፍት እንደሚያስረዱት ቤተ ክርስቲያን ከተመሠረተችበት ጊዜ ጀምሮ ከፈተና ተለይታ አታውቅም፡፡ ጌታን የሰቀሉ አይሁድ ደቀመዛሙርቱን በእርሱ ስም እንዳያስተምሩ ለማድረግ በማስፈራራት ብዙ ጥረዋል፤ አስረዋቸዋል፣ ገርፈዋቸዋል፣ አሳደዋቸዋል፣ ገድለዋቸዋል፡፡ ሐዋ.ሥ 4፥17-21 ነገር ግን ቤተ ክርስቲያን በአለት ላይ የተመሠረተችና በመንፈስ ቅዱስ የምትመራ ስለሆነ ሥራዋ አልተቋረጠም፤ ተከታዮቿም አልጠፉም ዕለት ዕለት ይበዛሉ እንጂ፡፡ ማቴ. 16፥18
ቤተ ክርስቲያን በዘመነ ሐዋርያት፣ በዘመነ ሰማእታትና በዘመነ ሊቃውንት እንደጊዜው የተለያየ መከራና ፈተና አሳልፋለች፡፡ የቤተ ክርስቲያን ጠላት የሆነው ዲያብሎስ ጥንት በአይሁድ፣ በሮማዊያን ነገሥታት፣ በአህዛብ እያደረ፤ ክርስቲያኖች በሃይማኖታቸው በመጽናታቸውና ቤተ ክርስቲያንን በማገልገላቸው ሰውነታቸው በሰም ተነክሮ በእሳት እንዲቃጠሉ፣ በቁርበት ተጠቅልለው ለአንበሳ እንዲሰጡ፣ በድንጋይ ተወግረው እንዲሞቱ፣ በስለት እንዲቀረደዱ፣ በሰይፍ እንዲቀሉ ያስደርግ ነበር፡፡ ክርስቲያኖችም በእምነታቸው እየጸኑ ከሞት የተረፉት፤ በዋሻ በግበበ ምድር እየሆኑ የቤተ ክርስቲያንን አገልግሎት ሲፈጽሙ ኖረዋል፡፡ ጌታ “የሲዖል ደጆች አያናውጧትም” ያላት ቤተ ክርስቲያን እስከ ዓለም ዳርቻ እየሰፋች የመሰረታትን ጌታ እያመሰገነች ትኖራለች፡፡ ቤተ ክርስቲያን አገልግሎቷን ለማሳካትና የዲያቢሎስን ሽንገላ ለመቋቋም በተለያዩ የአገልግሎት መስኮች ልጆቿን ታሰማራለች፡፡
የኢትዮጵያ ኦርቶዶክስ ተዋሕዶ ቤተ ክርስቲያን እውቅና ሰጥታ ልጆቿን ለአገልግሎት ካሰማራችባቸው መንገዶች አንዱ የማኅበራት አገልግሎት ነው፡፡ በዚህ የማኅበራት አገልግሎት የዲያቢሎስን ፈተናና ሽንገላ ተቋቁመው በርካታ መንፈሳዊ ተግባራትን እያበረከቱ ከሚገኙ ማኅበራት መካከል ማኅበረ ቅዱሳን አንዱ ነው፡፡
ማኅበረ ቅዱሳን በቅዱስ ሲኖዶስ ፈቃድ ከ22 ዓመታት በፊት ቅርጽ ይዞ የተዋቀረና በቤተ ክርስቲያን ውስጥ አገልግሎቱን የሚፈጽምበት ደንብና ሥርዓት የተበጀለት ማኅበር ነው፡፡ አባላቱም የቤተ ክርስቲያኒቱ ልጆች የሆኑና በየአጥቢያቸው የልጅነት ግዴታቸውን እየተወጡ የሚገኙ ሲሆኑ በቅናተ ቤተ ክርስቲያን ተሰባስበው ለቤተ ክርስቲያን እድገት የሚያግዙ የትሩፋት ሥራዎችን የሚሠሩ ናቸው፡፡
ማኅበሩ በመተዳደሪያ ደንቡ ላይ ተለይቶ በተሰጠው ተግባር መሰረት፤ በከፍተኛ ትምህርት ተቋማት የሚማሩ ተማሪዎችን በየአጥቢያቸው አሰባስቦ፤ ከየሰንበት ትምህርት ቤቶቹ ጋር በመተባበር ትምህርተ ሃይማኖትን የሚያስተምር፣ አባላቱንና በጎ አድራጊ ምእመናንን በማስተባበር ስብከተ ወንጌል በሀገር ውስጥና በውጪው ዓለም እንዲስፋፋ የሚያደርግ፣ አድባራትና ገዳማት በልማት ራሳቸውን እንዲችሉ የሚያደረግ፣ የቤ ተክርስቲያናችን ሀብት የሆነው የአብነት ትምህርት እንዲጠናከርና ሊቃውንቱም ወንበራቸውን እንዳያጥፉ በመርዳት ከፍተኛ አስተዋጽኦ እያበረከተ ይገኛል፡፡
ይህ መንፈሳዊ ተግባር በቤተ ክርስቲያን በመተግበሩ፤ ቤተ ክርቲያንን የማይወዱና ውድቀቷን እንጂ ጥንካሬዋን የማይሹ አካላት የማኅበሩን አገልግሎት አልወደዱትም፡፡ ስለሆነም ቤተ ክርስቲያንን ለማዳከም ማኅበረ ቅዱሳንን ጠልፎ መጣል እንደ ዋነኛ ስልት አድርገው ቆርጠው መሥራት ከጀመሩ ውለው አድረዋል፡፡ እነዚህ አካላት ለዓላማቸው የሚጠቅም ሆኖ እስካገኙት ድረስ ማንኛውንም ነገር ይጠቀማሉ፡፡ በተለያየ ደረጃ ያሉ ሰዎችን በማሳሳት፣አሉባልታ በመንዛት፣የቤተ ክርስቲያን አባቶችን ጭምር በማሳሳት የሚፈልጉትን ተግባር ለመፈጸምና ለማስፈጸም ይተጋሉ፡፡ ማሩን በማምረር ወተቱን በማጥቆር- ደጋግመው እየወተወቱ ብዙ የዋሐንን የነርሱን የማደናቀፍ ተግባር ተባባሪ ለማድረግ ይጥራሉ፡፡
በጎ ነገር ሲሠራ በጠላት ዲያብሎስ በኩል እንቅፋት እንደሚቀመጥ ሁልጊዜ የታወቀ ነው፡፡ ፈተናውን ማለፍ መሰናክሉን መቋቋም ግን የአንድ ክርስቲያን ግዴታ ነው፡፡ ማኅበረ ቅዱሳንም እንደነዚህ ዓይነት ፈተናዎች ከቀድሞ ጀምሮ ሲያጋጥሙት ቢቆይም በአገልግሎቱ ምክንያት የመጡ መሆናቸውን በመገንዘብ በአባቶች ጸሎት፣ በእግዚአብሔር ኃይል አሸንፎ ላለንበት ዘመን ደርሷል፡፡ ወደፊትም በእግዚአብሔር ፈቃድ ይቀጥላል፡፡
ከላይ በጠቀስናቸው አካላት አማካኝነት አንዳንድ ወገኖቻችን ስለማኅበሩ የተሳሳተ መረጃ ሲደርሳቸው ቤተ ክርስቲያንን የጠበቁ መስሏቸው አገልግሎቱን የሚያደነቅፉና ጥሩ ባልሆነ ሁኔታ የሚፈርጁትን አካላት ወግነው ሲቆሙ ይታያሉ፡፡ እነዚህ አካላት ትክክለኛውን መረጃ ቢያገኙ፣ ቢያውቁና ቢገነዘቡ ከማኅበሩ ጋር የዓላማ ልዩነት ስለሌላቸው፤ አብሮ በፍቅር ቤተ ክርስቲያንን ለማገልገል ምንም የሚቸግራቸው ነገር የለም ብለን እናምናለን፡፡ ወደፊትም ከማኅበሩ ጋር አብረው ሊሠሩ የሚችሉ፣ የሚመክሩና የሚያስተካክሉ እንደሆኑ ማኅበሩ ያምናል፡፡ ካሁን ቀደምም እንዲህ ዓይኖቶቹን አካላት ባገኘ ጊዜ ሁሉ ማኅበሩ በማወያየቱና በማስረዳቱ የማኅበሩን አገልግሎት እየደገፉ የሚገኙ በርካታ ናቸው፡፡
ቤተ ከርስቲያንን በዓላማ የሚጠሉ ግን የማኅበሩን አገልግሎት ቢያውቁና ቢረዱትም የዓላማ ልዩነት ስላላቸው መቼም አገልግሎቱን በቀና አያዩትም፡፡ ዕለት ዕለት ለማደናቀፍ ይጥራሉ፡፡ በዚህም የተነሳ በአሁኑ ሰዓት በቤተ ክርስቲያን መዋቅር ውስጥ ሆነው ነገር ግን ቤተ ክርስቲያንን ጠልፈው ለመጣል የሚታገሉ፣ እንዲሁም ከቤተ ክርስቲያን በአፍኣ ሆነው እጃቸውን ባስረዘሙ አንዳንድ አካላት ማኅበሩ ፈተናዎች እየገጠሙት ነው፡፡
ለምሳሌም ያህል በአንዳንድ ሀገረ ስብከቶች በቅዱስ ሲኖዶስ ጸድቆ በተሰጠው የመተዳደሪያ ደንብ መሠረት በዋናነት የሚያስተባብረውን የግቢ ጉባኤ ተማሪዎች ሃይማኖታዊ ትምህርት እንዳያስተምር ሲከለክሉና ሲያቋርጡ ይታያሉ፡፡ ማኅበሩ አገልግሎት የሚሰጥባቸውን ማእከላት ቢሮዎች የሚዘጉ አንዳንድ አጥቢያዎችም ይስተዋላሉ፡፡ በተጨማሪም ማኅበሩ የሚያበረክተውን ሁለንተናዊ የቤተ ክርስቲያን አገልግሎት እንዲደናቀፍ የሚፈልጉ አካላትም በሕዝብ ጉባኤዎችና ስብሰባዎች ሳይቀር የማኅበሩን ስም እያነሱ ተገቢ ያልሆነና ማኅበሩን በፍጹም የማይገልጹ ቅጽሎችን እየሰጡ ለማስረዳት ሲሞክሩ ይስተዋላሉ፡፡
እነዚህ ለማሳያነት በተጠቀሱት የማኅበሩ ተግዳሮቶች መነሻነት በአንዳንድ ግለሰቦች አማካይነት መዋቅሮችን አላግባብ በመጠቀም የግለሰቦቹን ምኞት ከግብ ለማድረስ የሚሠሩና ጥንቃቄ ያልታከለባቸው እርምጃዎች እንጂ የቤተ ክርስቲያን ወይም የመንግሥት ውሳኔ ነው ብለን አናምንም፡፡ ስለዚህ ማኅበረ ቅዱሳን የቤተ ክርስቲያን አካል እንደመሆኑ ፈተና ስለማይለየው ስለሚያጋጥሙት ፈተናዎች በጸሎት፣ የሚመለከታቸው አካላት በማስረዳትና በመወያየት፣ እንዲሁም በመታገስ አልፎ በኢየሱስ ክርስቶስ ደም የተመሰረተችውን ቅድስት ቤተ ክርስቲያንን እግዚአብሔር እስከፈቀደበት ጊዜ ድረስ ያገለግላል፡፡
ማኅበሩ ፈተና ሲያጋጥመው መንፈሳዊ ማኅበር እንደመሆኑ መፍትሔ ለማግኘት የሚሄድባቸው መንገዶች ሁልጊዜም የታወቁ ናቸው፡፡ ችግሮች ሲመጡ ጊዜያዊና በእግዚአብሔር ኃይል በቀላሉ ሊፈቱ የሚችሉ መሆናቸውን በመረዳት በጥበብና በትዕግስት ከሚመለከከታቸው አካላት ሁሉ ጋር እየተወያየ ይፈታል፡፡ የችግር አፈታቱ ሥርዓት መንፈሳዊነትን የተከተለ በመሆኑ ሥጋዊ አስተሳሰብን ሳይጨምር ሃይማኖታዊ ፈተና ሲመጣ ማሸነፊያው ሃይማኖታዊ ኃይል ነው ብሎ ያምናል፡፡ እርሱም እግዚአብሔርን አጋዥ አድርጎ በጾምና በጸሎት በትዕግስትና በጽናት፤ እግዚአብሔርን በመጠየቅ ነው፡፡
በማርቆስ ወንጌል ላይ እንደምናገኘው፡- (ማር. 4፡37) “ብርቱ ዐውሎ ነፋስም ተነሣና ውኃ በታንኳይቱ እስኪሞላ ድረስ ማዕበሉ በታንኳይቱ ይገባ ነበር። እርሱም በስተኋላዋ ትራስ ተንተርሶ ተኝቶ ነበር፤ አንቅተውም። መምህር ሆይ፥ ስንጠፋ አይገድህምን? አሉት። ነቅቶም ነፋሱን ገሠጸው ባሕሩንም። ዝም በል፥ ፀጥ በል አለው። ነፋሱም ተወ ታላቅ ፀጥታም ሆነ። እንዲህ የምትፈሩ ስለ ምን ነው? እንዴትስ እምነት የላችሁም? አላቸው። እጅግም ፈሩና። እንግዲህ ነፋስም ባሕርም የሚታዘዙለት ይህ ማን ነው? ተባባሉ።” ይላል፡፡ በታንኳይቱ የተመሰለችው ቤተ ክርስቲያን በፈተና ልትናወጥ ትችላለች፡፡ እንዲህ ባለ ጊዜ በውስጧ ያለውን፣ ነገር ግን እኛ የድርሻችንን እስክንወጣ ድረስ የሚጠብቀውንና ዝም ያለ (የተኛ) የሚመስለውን ጌታችን ኢየሱስ ክርስቶስን በጸሎት መጠየቅ ያስፈልጋል፡፡ ፈተናን ጸጥ የሚያደርግ አምላክ እንደምናመልክ ልንዘነጋ አይገባምና ፡፡
ማኅበሩ በቤተክርስቲያንም ሆነ በማኅበራችን ዙሪያ ስላሉ ነገሮች ማንኛውንም መረጃ የሚያስተላልፈው በራሱ ሚዲያና በመተዳደሪያ ደንቡ መሠረት ሥርዓት ባለው መልኩ በሚመለከታቸው የማኅበሩ ኃላፊዎች በኩል እንደሆነ የታወቀ ነው፡፡ ከዚህ ውጭ በሆነ መንገድ የሚተላለፍ ልዩ ልዩ መረጃዎችንና ሀሳቦችን በመያዝ ማኅበሩን በተመለከተ የግል ሀሳብንና ተግባርን ማንጸባረቅ አግባብ አለመሆኑን ሁሉም አካላት ሊያውቀው ያስፈልጋል፡፡
ማኅበራችን ማኅበረ ቅዱሳን ዓላማን ግብ ያለው በመሆኑ በጊዜው በሚታዩ ጥቅመኞችና አጽራረ ቤተ ክርስቲያን ሁከት ሳንዘናጋ የወንጌል ተልእኳችንን በጥበብና በትዕግስት ከግብ ማድረስ ይገባናል እንላላን፡፡ ስለዚህ ሐዋርያው ያዕቆብ የእምነታችሁ መፈተን ትዕግሥትን እንዲያደርግላችሁ እወቁ፡፡ ያዕ.1፡2 እንዳለ ስለ እምነታችንና ስለቤተ ክርስተያናችን የምናደርገውን አገልግሎት ፈታኙ ዲያብሎስ ሊያደናቅፍ ሠራዊቶቹን ቢያሰማራም እግዚአብሔር አምላካችንን ትዕግስትንና ጽናትን እንዲሰጠን ፈተናውንም እንዲያሳልፍልን በጽናት እንለምነው፡፡- እርሱ በሰው ዘንድ የማይቻለውን እንድንችል ማድረግ ያውቅበታልና፡፡ ለዚህም የቅዱሳን አምላክ እግዚአብሔር ይርዳን፡፡
ወስብሐት ለእግዚአብሔር

18/07/2016

“ገድለ ቅዱሳን የወንጌል ትርጓሜ ነው፤”(ክፍል፡-፪፤) - -“እጅህ ብታሰናክልህ ከአንተ
ቈርጠህ ጣላት፤”ማቴ፡፲፰፥፰። - - በወንጌል እንደተጻፈ፥ይኸንን የጌታ ቃል በገድሉ
የፈጸመው ሊቀ ጳጳሱ አትናቴዎስ ነው።የአንፆ ኪያው ሊቀ ጳጳስ አባ አትናቴዎስ፥ወደ
ክርስትና ሕይወት ከመጠራቱ በፊት፥ሃይማኖት የሌለው አረማዊ ነበረ።በኋላ ግን
ተምሮ፥አምኖ፥ተጠምቆ ክርስቲያን በመሆን፥ለሊቀ ጵጵስና በቅቶአል። (በአረማዊነት
የኖረ ሰው ከተጠመቀ በኋላ ንጽሕ ጠብቆ ከኖረ፥እንደ ድንግል ስለሚቆጠር፥ጵጵ ስና
ይሾማል።) በሀገራቸው አዲስ የተሾመ ሊቀ ጳጳስ፥ሰባት ቀን በተከታታይ ቀድሶ
ያቆርባል። በዚያ ልማድ በመጀመሪያው ቀን ቀድሶ፥አቍርቦ እየዞረ በሚባርክበት ጊዜ፡-
ጥንት በአረማዊነት ሳለ በግብር የምታውቀው ሴት፥እርሷ መሆኗን እንዲለያት ብላ እንደ
ተሸፋፈነች እጁን ነክሳ አቆሰለ ችው።ወዲያው የዝሙት ፆር ተፈታተነውና
ተቸገረ።በኅሊናውም፡- “ከዚህ ያደረሰችኝ ይህች እጄ አይደለችምን? እጄን ባልነከስ
ኖሮ፥እንዲህ ያለ ከባድ ፈተና ውስጥ አልገባም ነበር።” ብሎ አሰበ። አስቦም አልቀረ
ወደ ግምጃ ቤት ገብቶ፥እጁን ቆርጦ ጣላትና ከትራሱ ስር አስቀመጣት።ከዚህ በኋላ
መቀደስ ስላልቻለ፥ቍስሉን እያስታመመ ከበዓቱ ተከተተ።ካህናቱም እየተመላለሱ፥ “እንደ
ሥርዓቱ ቀድስልን፤” ቢሉት፥ዛሬ “አይቻለኝም፤”እያለ በተደጋጋሚ መለሳቸው።በዚህም
ምክንያት ባልገባቸው ምሥጢር፡-“ወደ ቀደመ ግብሩ ወደ አረማዊነቱ ተመልሶ ቢሆ ን
ነው፤” ብለው በሐ ሜት የሚጐዱ ሆኑ።ሐሜት ታላቅ ኃጢአት ነው፤ “አፍህ ክፋትን
አበዛ፥አንደበትህም ሽንገላን ተበ ተበ።ተቀምጠህ ወንድምህን አማኸው፥ለእናትህም ልጅ
ዕንቅፋት አኖርህ። . . .ባልንጀራውን በቀ ስታ የሚያማን እርሱን አሳደድሁ፤. .ሐሜትንም የሚገልጥ ሰነፍ ነው።. . .ወንድምም ሁሉ ያሰና ክላልና፥ባልንጀራም ሁሉ
ያማልና፤እናንተ ሁሉ ከባልንጀሮቻችሁ ተጠንቀቁ፥በወንድሞቻችሁ አትታ መኑ።ሰውም
ሁሉ ባልንጀራውን ያታልላል፥በእውነትም አይናገርም፤ሐሰትን መናገርንም ምላሳ ቸው
ተምሮአል፥ክፉንም ለማድረግ ይደክማሉ።ማደሪያህ በሽንገላ መካከል ነው፥ከሽንገላም
የተነሣ እኔን ያውቁኝ ዘንድ እንቢ ብለዋል፥ይላል እግዚአብሔር።”የሚል አለ።መዝ፡
፵፱፥፳፤፻፩፥፭፣ምሳ፡፲፥፲፰፣ኤር፡፱፥፬።ሊቀ ጳጳሱ አቡነ አትናቴዎስ፡- ካህናቱ በሐሜት
እንደተጐዱ ባወቀ ጊዜ፥ ከሥዕለ ማርያም ስር ተደፍቶ ወደ እመቤታችን ቢያመለክት
ብርህት እጅ ቀጥላለታለች።በማግስቱም ገብቶ ሲቀድስ፥የእጁ ብርሃን ዓይናቸውን
እየበዘበዘ (እያጥበረበረ) የማያሳያቸው ሆነ።ከቅዳሴ ውጭ ሲሆን፥ካህናቱ
ተሰብስበው፥“አባታችን ንገረን፥ ምሥጢሩ ምንድነው?”ቢሉት፥“የትራሴን ምንጣፍ
ግለጡት፤” አላቸው።ቢገልጡት የተቆረጠች እጁን ወድቃ አገኟት። በዚህን ጊዜ፡-
“ይህች የተቆረ ጠች እጅ የኔ ናት፥ይህች የምታበራው ደግሞ እመቤታችን የሰጠችኝ
ነው፤” ብሎአቸዋል። - -ዓይንህ ብታሰናክልህ አውጥተህ ከአንተ ጣላት፤”ማቴ፡፲፰፥፱።
- -ይኸንን ያደረጉ ብዙዎች ናቸው፥ከእነዚህም መካከል ስምዖን ጫማ ሰፊው አንዱ
ነው።ይህ ሰው ከፍጹምነት የደረሰ ጻድቅ ነው።ነገር ግን እንደ ተርታ ሰው ከመንገድ ዳር
ተቀምጦ ጫማ ይሰፋ ነበር።የሚያገኘውንም ገንዘብ በስውር ለጦም አዳሪዎች ይሰጥ
ነበር።ቀን ቀን ጫማ ሲሰፋ ይውላል ፥ሌሊት ሌሊት ደግሞ ሲመጸውት ሲሰግድ
ያድራል።የቅዱሳን ባላጋራቸው (ጠላታቸው)የሆነ ሰይ ጣን ፈተና አመጣበት።አንዲት
ሴተ ወይዘሮ ጫማ ስፋልኝ ብላ ቀረበችው።እርሷም አንዴ ሰፋ፥ አንዴ ጠበበ እያለች
(በምክንያት እየተመላለሰች)አስቸገረችው።ቢቸግረው፡-“ጫማውን እንደሆነ በሥርዓት
ሰፍቼ አስረክቤሻለሁ፥ለምን እየተመላለስሽ ሥራ ታስፈቺኛለሽ?”ሲል ጠየቃት።እር
ሷም፡- “ይህ ሁሉ (ጫማው ሰፋ ጠበበ ማለቴ)ለምክንያት ነው፥እኔስ የምመላለሰው
አንተን ብወድ ነው፥እጅግ መልከ መልካም ነህና፤” አለችው።እርሱም፡-“እኔ ለራሴ
ከመንገድ ዳር የተጣልሁ ደሀ ጫማ ሰፊ ነኝ፥ምኔ መልካም ነው?”ቢላት፥“ሁለንተናህ
መልካም ነው፥ይልቁንም በዓይንህ ይጸናብ ኛል፤” አለችው።መልሶም፡-“ዓይኔን
ትወጂዋለሽን?” ቢላት። “አዎን እወደዋለሁ፤” አለችው።በዚ ህን ጊዜ፡- “ይህማ ምን
ቁም ነገር አለው፥ውሀ አይደል?”ብሎ፥በጫማ መስፊያው አውልቆ ሰጥቷ ታል።
- -በሌላ በኵል ደግሞ፥ዓይን የተባሉ የትዳር ጓደኞች፥እጅ የተባሉ ልጆች፥እግር የተባሉ
ደግሞ ዘመድ አዝማድ ናቸው።ትርጉሙም፡-የትዳር ጓደኞቻችሁ ወይም ልጆቻችሁ
ወይም የሥጋ ዘመዶ ቻችሁ፥ያልሆነ ሥራ እናሠራችሁ ቢሏችሁ፥ዛሬ የእነርሱን ፈቃድ
ፈጽማችሁ፥በኋላ ተያይዛችሁ ወደ ገሃነም እሳት ከምትገቡ፥ዛሬ የእነርሱን ፈቃድ
አፍርሳችሁ፥የእግዚአብሔርን ፈቃድ ብቻ ፈጽማችሁ ፥እነርሱን
አጥታችሁ፥እግዚአብሔርን አግኝታችሁ፥ብቻችሁን ወደ መንግሥተ ሰማያት ብትገቡ ይሻ
ላችኋል፤ማለት ነው።ይኸንን ሁሉም ቅዱሳን አድርገውታል። - -“ይህን ተራራ፡-ከዚህ
ወደዚያ እለፍ ብትሉት ያልፋል፤”ማቴ፡፲፯፥፳።
-የጌታ ደቀ መዛሙርት፡-ከታቦር ተራራ ስር ያገኙትን በሽተኛ፥የተቆራኘውን ሰይጣን
አስወጥተው ሊፈውሱት አልቻሉም ነበር።ምክንያቱም፡-ኃይል የሚሆናቸው ጸጋ መንፈስ
ቅዱስ ገና አልተሰጣቸ ውም ነበርና ነው።ጌታ ክብረ መንግሥቱንና ግርማ መለኰቱን
በተራራው ራስ ገልጦ ሲመለስ፥ የበሽተኛው አባት ሰገደለትና፥“ጌታ ሆይ፥ልጄን
ማርልኝ፥በጨረቃ እየተነሣበት ይሰቃያልና፤ብዙ ጊዜ በእሳት፥ብዙ ጊዜም በውኃ
ይወድቃልና።ወደ ደቀ መዛሙርትህ አመጣሁት፥ሊፈውሱትም
አልቻሉም፤”አለው።እርሱም ደቀ መዛሙርቱን ስለ እምነታቸው መጉደል ከወቀሳቸው
በኋላ፥ጋኔ ኑን ገሥጾ ከበሽተኛው እንዲወጣ አድርጓል።ከዚህ በኋላ ደቀ መዛሙርቱ
ለብቻቸው ወደ ኢየሱስ ቀርበው፡-“እኛ ልናወጣው ያልቻልነው ስለ ምን ነው?” ብለው
ጠየቁት። ኢየሱስም፡-“ስለ እምነ ታችሁ ማነስ ነው፤ የሰናፍጭ ቅንጣት የሚያህል
እምነት ቢኖራችሁ፥ ይህን ተራራ፡-ከዚህ ወደዚያ እለፍ ብትሉት ያልፋል፤”የሚሳናችሁም
ነገር የለም።ይህ ዓይነት ግን ከጸሎትና ከጾም በቀር አይወ ጣም፤
አላቸው።”ይላል።ማቴ፡፲፯፥፲፬።ይህንን የጌታ ቃል ተፈጽሞ የምናየው፥በቅዱሳን ገድል
እንጂ፥ቅዱሳንን ከሚጠሉ መናፍቃን መካከል አንዳቸውም ፈጽመው ሊያሳዩን
አይችሉም።ይህ
በወንጌል የተጻፈ ቃል፥በአብርሃም ሶርያዊ ጊዜ ተፈጽሟል።ለሊቀ ጳጳሱ አንድ አይሁዳዊ
ወዳጅ ነበራቸው፥ሁለቱም (ሊቀ ጳጳሱም አይሁዳዊውም) ለንጉሡና ለመኳንንቱ
ወዳጆች ናቸው፥ወዳጆ ቸውን ለመጠየቅ በየፊናቸው (በየራሳቸው)ሲሄዱ፥እግረ
መንገዳቸውን የሃይማኖት ጉዳይ እያነሡ ይከራከራሉ።ነገር ግን፡-ሊቀ ጳጳሱ
አይሁዳዊውን፡-ሁል ጊዜ ምላሽ ያሳጡት ነበር።በዚህ የሚበ ሳጭ አይሁዳዊም፡-በሌላ
ጊዜ ለብቻው ገብቶ፥“እነዚህ ክርስቲያኖች እንጂል(ወንጌል) የምትባል መጽሐፍ
አለቻቸው፥በውስጧም፡-የሰናፍጭ ቅንጣት የምታህል እምነት ቢኖራችሁ፥ይህን ተራራ
ወደዚያ እለፍ ብትሉት ያልፋል፥የሚል ተጽፎ ይገኛል፥አድርጉ ቢሏቸው ግን
አይሆንላቸውም።” ብሎ፥በሊቀ ጳጳሱ ላይ ነገር ሠራ።ከዚህ በኋላ፡-ከሊቀ ጳጳሱ ጋር
ሲገናኙ ነገሩን እየረሳ፥ነገሩን ሲያስ ታውስ ደግሞ ሊቀ ጳጳሱን እያጣቸው፥ብዙ ቀን
ቆየ።ከዕለታት በአንዱ ቀን ግን፥ሊቀጳጳሱ ባሉበት ነገሩ ትዝ አለውና፡-“አባቴ
የምጠይቅህ ኑሮኝ፥አንተን ሳገኝህ ነገሩን እያጣሁት፥ነገሩ ትዝ ሲለኝ ደግሞ አንተን
እያጣሁህ ብዙ ቀን ቆየሁ።ዛሬ ግን አንተ ባለህበት ነገሩ ትዝ ብሎኛል።” አላቸው።
“ይኸንን ያህል ያስጨነቀህ ነገር ምንድነው?”ብለው ቢጠይቁት፥“ወንጌላችሁ፡-
የሰናፍጭ ቅንጣት የምታህል እምነት ያለው ሰው ተራራ ያነሣል፥ የምትለውን ማድረግ
ትችላላችሁን?”ሲል ጠየቃ ቸው። እርሳቸውም፡- “አዎን እንችላለን፤”አሉት። በዚህን
ጊዜ፡-“እንግዲያውማ የዚህ ሁሉ ክርስቲ ያን ሃይማኖት ቢደመር ከሰናፍጭ ቅንጣትነት
አልፎ ተራራ አያህልምን? አድርገህ አሳየኝ፤” ቢላ ቸው፥ሦስት ቀን ብቻ እንዲሰጣቸው
ጠይቀው፥ከእመቤታችን ሥዕል ስር ወድቀው አመለከቱ። እመቤታችንም፡-“ይህ ነገር
ለአንተ አይቻልህም፥የሚቻለው ለባለ አንድ ዓይኑ ለስምዖን ነው፤ ተርታ ሰው መስሎ
ከገበያ መካከል ተቀምጦ እንጨት ሲሸጥ ታገኘዋለህና ሂደህ ንገረው፥እሺ ብሎም ስለ
ማይቀበልህ፥እመቤታችን ነገረችኝ በለው፤” አለችው።ሄዶም አገኘውና እየፈራ በስተ
ኋላው ልብሱን ያዘው።ስምዖንም፡-አወቀብኝ ብሎ፥“ምን አድርግ ትለኛለህ? በሀገርህ
ድኃ አይኖር ምን?”አለው፥እጅግም ተቆጣ።በዚህን ጊዜ ሊቀ ጳጳሱ፡-እመቤታችን
እንደላከችውና የመጣበትንም ጉዳይ አስረዳው።
-ስምዖን ሁሉን ነገር ከሊቀ ጳጳሱ ከተረዳ በኋላ፥“እንኪያስ እኔን አትግለጠኝ፥ክርስቲያኑን
ከተራራው ፊት ለፊት፥አሕዛብን ደግሞ ከተራራው ጀርባ ሰብስበህ፥ካህናትንም አልብሰህ
ቆየኝ። አንተ እኔ የምሠራውን እያየህ ትሠራለህ፥ሕዝቡ ደግሞ አንተ የምትሠራውን እያዩ
ይሥሩ፤”አለው። ሊቀ ጳጳሱም የተባለውን ሁሉ አደረገ፤አርባ አንድ ኪራያላይሶን እያደረሱ
ሰግደው ሲነሡ፥ ተራ ራው ብድግ አለ።ተደፍተው ሲሰግዱ እየተመለሰ፥ከሰገዱበት
ሲነሡ ደግሞ ወደ ላይ እየተነሣ ተአ ምር ተደረገ።ክርስቲያኖችና አሕዛብም በተራራው
ስር ፊት ለፊት ተያዩ፥ይህ ተአምር የተደረገው ለሦስት ጊዜ ነው፥በአራተኛውም፡- እየወጣ
የሚያውካቸው ውኃ ስለ ነበረ፥ “ሂደህ ተጋረድላቸው፤” ቢለው፥ቦታውን ለቅቆ ሂዶ
ተጋርዶላቸዋል።

03/07/2016

“ ኩኑ ቅዱሳን እስመ ቅዱስ አነ” ዘሌ.19፡2
ቅዱሳን ማለት የተቀደሱ፣ የከበሩ፣ የተመሰገኑ፣ የተለዩ፣ የተመረጡ፣ ንጹሐንየሆኑ፣
የጠሩ….. ወዘተ ማለት ነው፡፡ ቅዱሳን በዚህ ስም የሚጠሩበት ከሰው ወይም
ከምድራዊ ባለሥልጣን የተቸሩት አይደለም፡፡
በሃይማኖት ጸንተው በምግባር ጐልምሰው የሥጋ ምኞታቸውን ጥለው አፍርሰው ሲገኙ
የቅድስና ባለቤት ቅዱስ እግዚአብሔር እነሱን /ቅዱሳንን/ መሣሪያ አድርጐ ኃይሉንና
ሥልጣኑን ቢገልጽባቸው ማኅደረ እግዚአብሔር መሆናቸው ይገለጻል፡፡ በዚህ ጊዜ
ቅዱሳን ይባላሉ፡፡ እሱ እግዚአብሐር ቅዱስ ተብሏልና የጌትነቱ መገለጫ የሆኑ ሁሉ
ቅዱሳን ይባላሉ ጻድቃን እንደመ ላእክት ውሉደ እግዚአብሔር ይባላሉ /ኢዮ.1፡6/፣
ሮሜ.8፡14/ ቅዱሳን ጻድቃን በግብር መላእክትን መስለው ሆነው የፈጣሪአቸውን ፈቃድ
ፈጽመው በመገኘታቸው ከዚህ ዓለም በመለየታቸው ቅዱሳን ሲባሉ የፈጣሪአቸውን
ሕያው መንግሥት ወራሾች ናቸውና ውሉደ እግዚአብሔር ይባላሉ፡፡ በሌላም ቃል ውሉደ
ብርሃን ይባላሉ፡፡ /ሉቃ.16፡8/ በዓለማቸው ይራቀቃሉና ይህን ዓለም ይጠሉታል፡፡
ውሉደ ሕይወት ይባላሉ ሞትንና የሞት ከተማ ይህን ዓለም ይንቃሉና በክብር ተነሥተው
ዳግመኛ ሲሞቱ የማይገባቸው ስለሆነ /ሉቃ.10፡30/ ውሉደ ጥምቀት ተብለዋል ሀብተ
ወልድና ስመ ክርስትናን ተጐናጽፈዋልና፡፡ ውሉደ መንግሥትም ተብለዋል የመንግሥተ
ሰማያት ባለቤቶች ናቸውና፡፡ በጸጋ እግዚአብሔር የበለጸጉ በመሆናቸው የእግዚአብሔር
አዕይንተ እግዚአብሔር ተብለዋል /መዝ.33፡15/
የፈጣሪአቸው ፈቃድ በተግባራቸው ስለሚታይ የእግዚአብሔር አዝነ ፈቃድ ወደ ጻድቃን
ነው፡፡ ልመናቸው ጾማቸው እንዲሁም ምጽዋታቸው ሁሉ የተወደደ መሥዋዕት ነው፡፡
ቅዱሳን በዓላማቸው ጾምን ግብዣ /ድግስ/፣ ለቅሶን ዘፈን፣ ደስታን ሐዘን አድርገው
በመኖራቸው ይህ ተለዋዋጭ ዓለም በየጊዜው የሚአቀርብላቸው መርዶ በእነሱ ዘንድ
ዋጋ የለውም ወይም ዋጋ አይሰጡትም፡፡ ዓለምም ለእነሱ የሚያቀርበው ዓለማዊ
የምኞት ስጦታ እንደ ኢምንት የተቆጠረ ነው፡፡ የእግዚአብሔር ገጸ መዓቱ ወደ
ዓለማውያን ሰነፎች እንደሆነ ገጸ ምሕረቱ ወደ ቅዱሳን ነው፡፡ ስለዚህ አማላጅነታቸው
ጸሎታቸው በጣም ጠቃሚ ነው፡፡ “አፍቅርዎ ለእግዚአብሔር ኲልክሙ ጻድቃኑ” ቅዱሳን
እውነትን ይዛችሁ ትሕትናን ተላብሳችሁ እግዚአብሔርን ውደዱት “እስመ ጻድቅ የሐስስ
እግዚአብሔር” እግዚአብሔር እውነትን ትሕትናን ይወዳልና፡፡ /መዝ.30፡23/ የቅዱሳን
ፍሬ ትሕትና ነው፡፡ በዓይነ ሕሊናቸው ፈጣሪአቸውን በዓይነ ሥጋቸው የእነሱን ምንነት
እንዲሁም የዓለምን ከንቱነት ይመለከታሉ፡፡
ፍሬ የያዘ ተክል ሁሉ ቁልቁል የተደፋ ነው፤ ትሕትናን ያስተምራል፣ የጻድቃን ምሳሌ
ነው፡፡ በፈሪሃ እግዚአብሔር ልቡ የተሰበረ እሱነቱን /ምንነቱን/ የመረመረ ሰው በዓይነ
ሕሊናው የፈጣሪውን ቸርነት በዓይነ ሥጋው የራሱን ውድቀት ይመለከታል፡፡ ይህ
አመለካከት ለጸጋ እግዚአብሔርና ለፍሬ ክብር ያደርሱታል፡፡ በመቅረዝ ላይ ያለች
መብራት መሰወር እንዳይቻላት የመቅረዙ ከፍታ የግድ እንደሚገልጻት በተራራ ላይ ያለች
ቤትም በእይታ እንደማትሰወር የተራራው ከፍታ እንደሚገልጻት በጥበበ እግዚአብሔር
ከብረው በጸጋ እግዚአብሔር ተውበው የሚኖሩ ቅዱሳን ጻድቃንም ደረጃ በደረጃ
ማዕረጋትን አልፈው ከመለኮት ባሕርይ ተካፍለው የተአምራት መገለጫ ተካፍለው
የተአምራት መገለጫ ይሆናሉ፡፡ “መንክር እግዚአብሔር በላዕለ ቅዱሳኑ” /መዝ.67፡
35/ “እግዚአብሔር በቅዱሳኑ በወዳጆቹ አድሮ የሚሠራው ሥራ ድንቅ
ነውን፡፡ /2ኛጴጥ.1፡3/ ቅዱሳን የጸጋ ተዋሕዶ ተዋሕደው ሲገኙ ሙት ሲሆኑ ሙታንን
ማስነሳት እውር ሲሆነ እውርን ማብራት፣ በዓለም ላይ ድንቅ ሥራቸው ይሆናል፡፡ የጸጋና
የክብር ተሸላሚዎች ሆነዋልና በዓለም ላይ ሳሉ የሚመጣባቸውን ፈተና ሁሉ ከምንም
ባለመቁጠር ተቋቁመው የጸጋ መቅረዝ ተቋሞች ይሆናሉ፡፡ በዚህም በአላሰለሰው
ሕይወታቸው የአንበሳ አፍ ዘጉ /ዳን.7፡1-28/ ውኃውን ወደ ኋላው መለሱ /ዘጸ.14፡
22/ ሰማይን አዘዙ /1ኛ ነገ.17፡1፣ ያዕ.5፡17/ ነበለባለ እዥሰት አበረዱ /ዳን.3፡
1-13/ የአብርሃም የይስሐቅ የያዕቆብ ወዳጅ እግዚአብሔር ከዘመድ ባዕድ ከሀገር
የሚኖሩትን በረድኤት ይቀበላል፣ ሥጋዊ ሀገረ ተድላን ጥለው ሓላፊ ጠፊ ምድራዊ
ምቾታቸውን ንቀው ጸጋውን የሚጠባበቁትን ሁሉ አብሮአቸው ይኖራል፡፡ ትዕግስትን
የጥዋት ቁርስ የቀን ምሳ የማታ እራት አድርገው የሚመገቡትን ሁሉ ቤተ መቅደስ
አድርጓቸው ይገኛል፡፡
ቅዱሳን በዚህ ዓለም ይጠበቡበታል፣ ወጥተው ወርደው እነሱነታቸውን ከስስት ኃጢአት
ጠብቀው ለወዲያኛው ዓለም ደግሞ በትዕግሥት ደጅ ይጠኑበታል፡፡ “አሪሃ
እግዚአብሔር ትፍስህተ ልብ ውእቱ ወይሁብ ሐሴተ ወያስተፌስህ ወያነውሀ መዋዕለ
ሕይወት፤ እግዚአብሔርን መፍራት የልብ ደስታ ነው፡፡ ፍጹም የሥጋና የነፍስን ደስታ
ይሰጣል በሕይወትም ያኖራል፡፡” “ለፈሪሃ እግዚአብሔር ይሴኒ ድሐሪቱ ወይትባረክ አመ
እለተ ሞቱ እግዚአብሐርን የሢፈራ ሰው ፍጻሜው ያምርለታል እንደ ኢዮብ ከደዌው
ተፈውሶ ልጅ ልጅ አይቶ ይሞታል /ኢዮብ.31፡16/ ይህ ሁሉ በረከት የቅዱሳን
የሁልጊዜ ፍሬ ነው፡፡
ቅዱሳን ሁል ጊዜ የሚሠሩት ሰማያዊ ድርብ ድርብርብ /እንደ ሐመረ ኖኅ/ በጸጋ ላይ
ጸጋ እየተጨመረላቸው ወደ 10ሩ መእረጋት ይወጣሉ፡፡ በያዙት ቀን መንገድም ኢዮባዊ
ትዕግስት አብርሃማዊ ሂሩት ይስሐቃዊ ፈቃደኛነት ያዕቆባዊ ቅን አገልግሎት ጠሴፋዊ
ሀዳጌ በቀልነት ሙሴአዊ ለወገን ተቆርቋሪነት እየጨመሩ በመኖራቸው ሳያውቁት
የፈጣሪአቸውን ኃይል የጌትነቱ የመለኮትነቱን ድንቅ ሥራ መገለጫዎች ይሆናሉ፡፡
ማዕረጋቸውን ከዚህ ይናገሩታል፡-
የንጽሐ ሥጋ ማዕረጋት 3 ናቸ ው እነሱም፡-
1. ጽማዌ
2. ልባዌ
3. ጣዕመ ዝማሬ ይባላሉ፡፡
የንጽሐ ነፍስ ማዕረጋት 4 ናቸው
1. አንብዕ
2. ኲነኔ
3. ፍቅር
4. ሁለት ናቸው፡፡
የንጽሐ ልቡና ማዕረጋት ናቸው እነሱም
1. ንጻሬ መላእክት
2. ተሰጥሞ
3. ከዊነ እሳት ናቸው፡፡
የንጽሐ ሥጋ ማዕረጋት
1. ማዕረገ ጽማዌ፡- ይህ ማዕረግ የመጀመሪያው ነውና ማስተዋል ውስጣዊ ትዕግስትን
ውስጣዊ ትህትና ውስጣዊ የራስ ሚዛንን ይዞ ማሰላሰል…… ወዘተ ይጀምራል፡፡ ከዚህ
ማዕረግ ሲደርሱ እግዚአብሔርን ብቻ መዘከር ይችሉ ዘንድ የዚህን ዓለም ውጣ ውረድ
ከማውራት ይከለከላሉ፡፡ በዚህ ማዕረግ መላእክት ሲወጡና ሲወርዱ ያያሉ፡፡ ነገር ግን
ለምን እንደሚወጡና እንደሚወርዱ አያውቁም፡፡ ዮሐንስ ሐጺር የሰፋውን ስፌት ገበያ
ላይ ለመሸጥ ተቀምጦ እያለ እርሱ ግን በተመስጦ እነ ቅዱስ ሚካኤልንና ቅዱስ
ገብርኤልን እንዲሁም ሌሎችን መላእክት በየማዕረጋቸው እያየ ሲያደንቅ ስፌቱን
የሚገዛ ሰው ቁሞ እንቅቡ ዋጋው ስንት ነው ብሎ ሲጠይቀው እርሱ የሚያየውን
የሚያይ መስሎት “ሚካኤልኑ የዓቢ ወሚመ አኮ ገብርኤል ሚካኤል ይበልጣል ወይስ
ገብርኤል” ብሎ በአንክሮ ጠየቀው፡፡ ይህን ሲለው ሰውየው ይሄስ እብድ ነው ብሎ
ትቶት ሄዷል፡፡
2. ማዕረገ ልባዌ፡ - ደግሞ ማስተዋል ልብ ማድረግ አሰሙኝ እንጂ ስሙኝ አለማለት
ልማር እንጂ ላስተምር አለማለት የተነገረው ትንቢትና ተግጻጽ ምዕዳን ሁሉ የራሱ
እንደሆኑ መገመት መመርመር ዓይነ ሥጋን ከመጽሐፍ ከስነ ፍጥረት ዓይነ ነፍስን
ከምስጢር….. ወዘተ ማዋል ነው፡፡ ወይም የእግዚአብሔርን ቸርነት ማድነቅ ስለሰው
ያደረገውን ውለታ ማሰላሰል ከሰማየ ሰማያት መውረዱን ከሰው መወለዱን በገዳም
መጾሙን መገረፉን ሥጋውን መቁረሱን ደሙን ማፍሰሱን መሰቀሉን መሞቱን መቀበር
መነሳቱን እያሰቡ ልብን በፍቅረ እግዚአበሔር መሰበር አንደበትን በመንፈሳዊ ሕይወት
መስበር ዓላማን በገጸ መስቀል/ትዕግሥት/ ማስተካከል የመሳሰሉት ናቸው፡፡
3. ማዕረገ ጣዕመ ዝማሬ፡- ከዚህ ደረጃ ሲደርስ አንደበትን ከንባብ ልቡናን ከምስጢር
ማቆራኘት ነው፡፡ ቅዱሳን ከዚህ ማዕረግ ሲደርሱ አንደበታቸው ምንም ዝም ቢል
በልባቸው ውስጥ ዝም አይሉም፡፡ ከአፍ እስትንፋስ ከአፋፍ ላይ ነፋስ እንደማይለይ ሁሉ
ከአንደበታቸው ትዕግስት ከእጃዋው ምጽዋት ከልቡናቸው ትሕትና ከሰውነታቸው ንጽሕና
አይለይም፡፡
4. የሚጸልዩትና የሚይነቡት ምስጢሩ እየገባቸው ስለሚያደርጉት አይሰለቻቸውም፡፡ ከዚህ
ማዕረግ የደረሰ አንደ ባሕታዊ ለብዙ ዘመናት አቡነ ዘበሰማያት /አባታችን ሆይ/ እያለ
ብቻ ሲኖር መልአክ መጥቶ ይትቀደስ ስምከ በል እንጁ ቢለው ኧረ ጌታዬ እኔስ አቡነ
የሚለው ኃይለ ቃል ምስጢሩና ጣዕሙ በአፌ እንደ ጨሙ እየሟሟ አልጠገበኝ ብሏል
እንዴት አድርጌ ወደፊት ልሂድ ብሎታል፡፡
የንጽሐ ነፍስ ማዕረጋት
1. ማዕረገ አንብዕ፡- ከዚህ ማዕረግ ሲደርሱ ቅዱሳን እግዚአብሔር ኢየሱስ ክርስቶስ
ለሰው ልጅ ያደረገውን ፍቅር እስከ ሞትና መቃብር የተጓዘውን የመከራ ጉዞ እያሰቡ
በአንጻሩም ምረረ ገሃነመ እሳትን ጣዕመ መንግሥተ ሰማያትን እያሰላሰሉ ውሉደ አዳም
ይህን ሁሉ መከራ ባለ መገንዘብ ወደ ሰፊው የፈቃደ ሥጋ ሲጓዝ በማየታቸው ሲአለቅሱ
ይታያል፡፡ ያለምንም መሰቀቅ ሲአለቅሱ እንባቸው እንደ ምንጭ ይፈሳል፡፡ እንደ ሰን ውኃ
ይወርዳል ይኸውም ለዚህ ዓለም ብለው የሚአለቅሱት ልቅሶ ፊትን ያንጣጣል ዓይንን
ይመልጣል የቅዱሳን ልቅሶ ግን ፊትን ያበራል ኃጢአትን ያስወግዳል እርጥብ እንጨት
ከእሳት ጋር በተያያዘ ጊዜ እንጨቱ ከነበልባለ እሳት ሲዋሐድ እንጨቱ እርጥብነቱን ትቶ
ውኃውን በአረፋ መልክ እያስወገደ ይነዳል፡፡ ቅዱሳንም በግብር/በሥራ/ ከመለኮት ጋር
ሲዋሐዱ የዚህ ዓለም ምስቅልቅል ሥራ በሰማያዊ የረጋ ሕይወት ተለውጦ
አሠራራቸው አካሄዳቸው ፍጹም ሕይወታቸው መልአካዊ ይሆናል፡፡
2. ማዕረገ ኲነኔ፡- ከዚህ ማዕረግ ላይ ሲደርሱ ሥጋዊ ፈቃድ ሁሉ ለነፍስ ፈቃድ ይገዛል
ነፍስ በሥጋ ባሕርያት ላይ ትሰለጥናለች ምድራዊ /ሥጋዊ/ ምኞት ሁሉ ይጠፋና
መንፈሳዊ /ነፍሳዊ/ ተግባር ሁሉ ቦታውን ይወርሳል ያለምንም ማወላወል መንፈሳዊ
ተግባር ሁሉ ይከናወናል፡፡
3. ማዕረገ ፍቅር፡- ከዚህ ማዕረግ ሲደርሱ ውሉደ እግዚአብሔር ቅዱሳን እንደ
ፈጣሪአቸው ሁሉን አስተካክለው በመውደድ ይመሳሰላሉ አማኒ መናፍቅ ኃጥእ ጻድቅ
ዘመድ ባእድ ታላቅ ታናሽ መሃይም መምህር ሳይሉ አስተካክለው በመውደድ
የእግዚአብሔር ልጆች መሆናቸውን ይገልጻሉ፡፡
4. ማዕረገ ሁለት፡- ቅዱሳን ከዚህ ማዕረግ ላይ ሲደርሱ ባሉበት ሆነው ሁሉን ማየት
መረዳት ይችላሉ፡፡ ጠፈር ደፈር ሳይከለክላቸው ርቀት ሳያግዳቸው ሁሉን በሁሉ
ይመለከታሉ፡፡
የንጽሐ ልቡና ማዕረጋት
1. ንጻሬ መላእክት
2. ተሰጥሞ
3. ከዊነ እሳት ናቸው፡፡
1. ማዕረገ ንጻሬ መላእክት፡- ከዚህ ማዕረግ ሲደርሱ የመላእክት መውጣት መውረድ
ማየት ተልእኮአቸውን ያለምንም አስተርጓሚ መረዳት ማነጋገርና ማማከር የመሳሰሉትን
መፈጸም፤ ለምሳሌ እንደ ዮሐንስ አፈወርቅ መልአኩን 10 ዓመት ማቆም ነው፡፡
2. ማዕረገ ተሰጥሞ፡- ከዚህ ማዕረግ ሲደረስ በባህረ ብርሃን መዋኘት ባሉበት ሆኖ ወደ
ላይም ወደታችም መመልከት መቻል….. ወዘተ ናቸው፡፡
3. ማዕረገ ከዊነ እሳት /ነጽሮተ ሥሉስ ቅዱስ/፡- የፈጣሪ ቤተ መቅደስ ሆኖ ጸጋ
በተዋሕዶ ከመላእክት ጋር ሆኖ ረቆ ማመስገን ያሉበትን ሥጋ በብቻው ማየት በአካለ
ነፍስ ሰማየ ሰማያትን መጐብኘት ገነት ውስጥ መግባት ናቸው፡፡
እነዚህም የቅዱሳን ማዕረጋት 10 ናቸው፡፡ /2ኛ ጴጥ.1፡4-10፣ ዮሐ.1፡40/ የአስሩ
ማዕረጋት ምሳሌዎች የአስሩ ቃላት፡፡ /ዘጸ.20፡3-12፣ ዮሐ.13፡17/
በመጨረሻም ቅዱሳን የቅዱስ እግዚአብሔር ቤተ መቅደሶች ናቸው ኑሮአቸውም ቅዱስ
ነው፡፡
የቅዱሳን በረከታቸው አይለየን፡፡ አሜን፡፡

Address


Website

Alerts

Be the first to know and let us send you an email when Teppi semaetu qidus giorgis bete kistian posts news and promotions. Your email address will not be used for any other purpose, and you can unsubscribe at any time.

  • Want your business to be the top-listed Health & Beauty Business?

Share