11/05/2026
5ኛው ሃገር አቀፍ የጤና መረጃ እና የዲጂታል ጤና ሳምንት መካሄድ ጀመረ
5ኛው ሃገር አቀፍ የጤና መረጃ እና የዲጂታል ጤና ሳምንት "በጤና መረጃ እና በዲጂታል ጤና ፈጠራዎች ላይ ዘላቂ ኢንቨስትመንት በማድረግ የጤና ትሩፋትን ማፋጠን" በሚል መሪ ቃል መካሄድ ጀምሯል።
መረጃን መሰረት ያደረገ የጤና ስርዓት መገንባት የጤና ስርዓትን የምናሳድግበት ዋነኛው ምሰሶ መሆኑን በመደረኩ የመክፈቻ ንግግራቸው የገለጹት የጤና ሚኒስትር ዶ/ር መቅደስ ዳባ፤ ሁሉን አቀፍ የጤና አገልግሎት ለመስጠት መረጃ መሰረት ነው ብለዋል። ለዚህም የመረጃ ስርዓቱን እስከ ታች ድረስ በመዘርጋት የተቀናጀ እና የተናበበ ስርዓት መዘርጋት መቻሉን አስረድተዋል።
የተቋማት የተገልጋይ መረጃን በአንድ ቋት የማሰባሰብ ስራ እየተሰራ መሆኑን የገለጹት ዶ/ር መቅደስ ዳባ: ለዚህም በበርካታ ተቋማት ከወረቀት ነፃ የኤሌክትሮኒክ ጤና መረጃ (EMR) አሰራር መተግበር መጀመራቸውን ገልጸዋል።
የመረጃ ስርዓቱን በጤና ዘርፍ ለማዘመን ከዩኒቨርሲቲዎች ጋር በመተባበር የጤና መረጃን በካሪኩለም ውስጥ በማካተት ብቁ የሰው ኃይል ለመፍጠር እየተሰራ መሆኑንም አክለዋል።
በጤናው ዘርፍ የተገኙ ውጤቶችን ለማስቀጠል የጤና መረጃ እና ዲጂታል ጤና ፈጠራዎች ላይ ዘላቂ ኢንቨስትመንት ማድረግ አስፈላጊ መሆኑን የተናገሩት በጤና ሚኒስቴር የስትራቴጂክ ጉዳዮች ስራ አስፈጻሚ ዶ/ር ሙሉቀን አርጋው ሲሆኑ: ለአንድ ሳምንት በሚቆየው የጤና መረጃ እና ዲጂታል ጤና ሳምንት ከባለድርሻ አካላት ጋር የተለያዩ ውይይቶች ይደረግብታል ብለዋል።
በመድረኩ በጤናው ዘርፍ የተሻለ የጤና መረጃ አፈጻጸም ላስመዘገቡ ወረዳዎች እና ዩኒቨርሲቲዎች እውቅና ተሰጥቷል።
Ministry of Health,Ethiopia
Dr Mekdes Daba, Minister of Health