27/04/2026
ፅቡቕ ዉሳነ እዩ።
ብደላላ ዝግበር ናይ ደገ ሕክምና ግልጋሎት ብሰብ ሞያ ጥዕና እምበር ብደላላ ክኾን የብሉን።
ለህክምና ውጭ አገር ለመሄድ ፈቃድ የሚጠይቅ ታካሚ እንደ ህክምናው አይነት ከ 500 ሺ እስከ 1 ሚሊየን ብር በባንክ ሂሳቡ መኖሩን የሚያረጋግጥ ሰነድ እንዲያቀርብ የሚያስገድድ መመሪያ ወጥቷል።
የኢትዮጵያ ጤና ሚኒስቴር ወደ ውጭ አገር ሄደው ለሚታከሙ ዜጎች ጥራት ያለው፣ ደህንነቱ የተጠበቀና ክብራቸውን የሚመጥን የሕክምና አገልግሎት እንዲያገኙ ያስችላል ያለውን "የውጭ አገር የሕክምና አገልግሎት ቅብብሎሽ ሥርዓት ማስፈፀሚያ መመሪያ ቁጥር 1128/2018" አውጥቷል።
ይህ አዲስ መመሪያ በዋነኝነት የታካሚዎችን እንግልት ለመቀነስ፣ በዘርፉ የሚታዩ የአሰራር ክፍተቶችን ለመሙላት እና በሕክምና ስም የሚከናወኑ ሕገ-ወጥ ተግባራትን ለመቆጣጠር ታስቦ የተዘጋጀ ነው ተብሏል።
መመሪያው በጤና አገልግሎት አስተዳደርና ቁጥጥር አዋጅ ቁጥር 1362/2017 መሰረት የወጣ ሲሆን፣ ከሕክምና ቦርድ አሰራር ጀምሮ እስከ ወኪል ተቋማት የብቃት ማረጋገጫ ድረስ ያሉ ሂደቶችን በዝርዝር ይደነግጋል።
በመመሪያው መሰረት አንድ ታካሚ ወደ ውጭ አገር ሄዶ እንዲታከም የሚፈቀድለት:-
• የሚፈለገው የሕክምና ዓይነት በሀገር ውስጥ የማይሰጥ መሆኑ፣
• ለምርመራ የናሙና ዝውውር የማይቻል መሆኑን
• በከፍተኛ ወረፋ ምክንያት የታካሚው ሕይወት አደጋ ላይ የሚወድቅ መሆኑ ወይም
• ለክትትል የሚሄድ መሆኑን በሚመለከተው አካል ወይም በሕክምና ቦርድ ሲረጋገጥ ብቻ ነው።
ይህን ውሳኔ የሚሰጠው የሕክምና ቦርድ በሆስፒታሉ ሜዲካል ዳይሬክተር የሚመራና ከ3 እስከ 5 አባላት ያሉት ሆኖ በየሳምንቱ እየተሰበሰበ ውሳኔ እንደሚያስተላልፍ በመመሪያው ተመላክቷል።
ወደ ውጭ አገር ለመሄድ ፈቃድ የሚጠይቅ ታካሚ የጸደቀ የቦርድ ማስረጃ፣ የታደሰ መታወቂያ ወይም ፓስፖርት ማቅረብ ይኖርበታል።
በተጨማሪም ለሕክምናው የሚያስፈልገውን ወጪ ለመሸፈን በባንክ ሂሳቡ ቢያንስ 500,000 (አምስት መቶ ሺ) ብር፣ ለንቅለ ተከላ (Transplant) ሕክምና ከሆነ ደግሞ 1,000,000 (አንድ ሚሊዮን) ብር መኖሩን የሚያረጋግጥ ሰነድ ማቅረብ እንዳለበት መመሪያው ያዝዛል።
ለንቅለ ተከላ ሕክምና የሚሄዱ ታካሚዎች ከለጋሹ ጋር ያላቸውን ስምምነትና የለጋሹን የጤና ሁኔታ የሚያሳዩ ተጨማሪ ሰነዶችን ማቅረብ ይኖርባቸዋል።
ታካሚዎችን ከውጭ አገር የሕክምና ተቋማት ጋር የሚያገናኙ ወኪሎች የጤና ባለሙያ መሆን እንዳለባቸውና ከሚኒስቴሩ የብቃት ማረጋገጫ ምስክር ወረቀት ማግኘት እንዳለባቸው ተደንግጓል።
ወኪሎች ለታካሚው ስለሚሰጠው አገልግሎት የተጋነነ መረጃ መስጠት የተከለከለ ሲሆን፣ በየሩብ ዓመቱ ለሚኒስቴሩ የስራ አፈፃፀም ሪፖርት የማቅረብ ግዴታ ተጥሎባቸዋል።
ውጭ አገር የሚገኘው የጤና ተቋም ለሚሰጠዉ የህክምና አገልግሎት ለሚከሰት ጥራት ደረጃ ጉድለት፤የህክምና ስህተት፣ የሙያ ግድፈት እና መሰል ድርጊቶች ለታካሚው ካሳ መክፈል እንዳለበት ተደንግጓል።
ካሳ የሚከፍለው "ተቋሙ" ቢሆንም፣ ወኪሉ ይህ ተጠያቂነት ያለበትን ተቋም የመምረጥና ጉዳዩን የማስፈጸም "ኃላፊነት" ይኖርበታል።
መመሪያውን በሚጥሱ ወኪሎች ላይ ሚኒስቴሩ እንደ ጥፋቱ ክብደት የጽሁፍ ማስጠንቀቂያ፣ የብቃት ማረጋገጫን ማገድና እስከ መሰረዝ የሚደርስ እርምጃ ይወስዳል።
በተለይም ሀሰተኛ ማስረጃ ማቅረብ፣ የታካሚውን ደህንነት አደጋ ላይ መጣልና ከሚኒስቴሩ እውቅና ውጭ መንቀሳቀስ ለብቃት ማረጋገጫ መሰረዝ ዋና ምክንያቶች ናቸው።
ይህ መመሪያ በፍትሕ ሚኒስቴር ተመዝግቦ መጽደቁን ጤና ሚኒስቴር ለቲክቫህ ኢትዮጵያ አረጋግጧል።
ቲክቫህ ኢትዮጵያ
ሚያዚያ 18 ቀን 2018 ዓ/ም